Quantcast
Channel: ዜና
Viewing all 1779 articles
Browse latest View live

የአፍሪካ ኅብረት ዋናው የስብሰባ አዳራሽ በኔልሰን ማንዴላ ስም ተሰየመ

$
0
0
የአፍሪካ ኅብረት ዋናው የስብሰባ አዳራሽ በኔልሰን ማንዴላ ስም ተሰየመ

ከሁለት ዓመት በፊት በቻይና መንግሥት የ200 ሚሊዮን ዶላር ወጪ በተገነባው የአፍሪካ ኅብረት ሕንፃ የሚገኘው ታላቁ የስብሰባ አዳራሽ፣ ለቀድሞው የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚዳንት ኔልሰን ማንዴላ ማስታወሻ እንዲሆን ተወሰነ፡፡ 

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ማክሰኞ ረፋድ ላይ በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ አልጄርያ ባቀረበችው ሐሳብ መሠረት ዋናው የኅብረቱ የስብሰባ አዳራሽ በቅርቡ ከዚህ ዓለም ለተለዩት የደቡብ አፍሪካ በቀድሞው ፕሬዚዳንት ኔልሰን ማንዴላ ስም እንዲሰየም በኅብረቱ መሪዎች በዝግ ስብሰባ መወሰኑን ተናግረዋል፡፡ 

በዓለም የነፃነት ታጋይ ተምሳሌት የሆኑትና የወጣትነት ዘመናቸውን በሙሉ በእስር ያሳለፉት ኔልሰን ማንዴላ፣ በደቡብ አፍሪካ የነበረው የአፓርታይድ ሥርዓት እንዲንኮታኮት በቁርጠኝነት የታገሉ ናቸው፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ የአፍሪካ ኅብረት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች በባህር ዳር ባካሄዱት ስብሰባ ለኅብረቱ የፀጥታው ምክር ቤት ኢትዮጵያና ታንዛንያን ከምሥራቅ አፍሪካ መምረጣቸውን አምባሳደሩ ዲና አክለው ገልጸዋል፡፡  

 

ጐፋ ገበያ ማዕከል ላይ በደረሰ የእሳት ቃጠሎ 19 መደብሮች ወደሙ

$
0
0
ጐፋ ገበያ ማዕከል ላይ በደረሰ የእሳት ቃጠሎ 19 መደብሮች ወደሙ

-በገበያ ማዕከሉ የእሳት ቃጠሎ ሲደርስ ለዘጠነኛ ጊዜ መሆኑ ታውቋል

በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ወረዳ 6 ልዩ ቦታው ቄራ ጐፋ የገበያ ማዕከል ላይ በደረሰ የእሳት ቃጠሎ 19 መደብሮች ሙሉ በሙሉ ወደሙ፡፡ 

ጥር 26 ቀን 2006 ዓ.ም. ከሌሊቱ 7፡15 ሰዓት ላይ የእሳት ቃጠሎው እንደተከሰተ የገለጹት፣ የእሳትና ድንገተኛ አደጋ መከላከልና መቆጣጠር ባለሥልጣን ኮሙዩኒኬሽን ኦፊሰር አቶ ንጋቱ ማሞ ናቸው፡፡ የእሳቱ መነሻ ምክንያትና በንብረት ላይ የደረሰው የጉዳት መጠን አለመታወቁን ተናግረዋል፡፡

በቄራ ጐፋ የገበያ ማዕከል ውስጥ ቁጥራቸው 500 የሚደርሱ ነዋሪዎችና ነጋዴዎች መኖራቸውን የገለጹት አቶ ንጋቱ፣ ከቤቶቹና ከሱቆቹ አሠራር አኳያ ሲታይ 19 መደብሮችና መኖሪያ ቤቶች ብቻ ተቃጥለው ሌሎቹ መትረፋቸው አስገራሚ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ቤቶቹ ከተሠሩበት ግብዓትና መቀራረብ አኳያ መሆኑን አክለዋል፡፡ 

ከ53 ሺሕ ሊትር በላይ ውኃ በመርጨትና ሌሎች የማጥፊያ ዘዴዎችን በመጠቀም በ1፡30 ሰዓት ውስጥ እሳቱን ለመቆጣጠር መቻሉን ኦፊሰሩ ተናግረዋል፡፡ ቤቶቹ ቆርቆሮ በቆርቆሮ ሆነው ከመሠራታቸው በተጨማሪ፣ እጅግ በጣም የተጠጋጉና መደብሮቹም ውስጥ ለእሳት መቀጣጠል ምቹ የሆኑ ሸቀጣ ሸቀጦች በመኖራቸው ምክንያት ለማጥፋት አስቸጋሪ እንደነበር ጠቁመዋል፡፡

ባለሥልጣኑ የግምት ባለሙያ ባይኖረውም ከተረፈው ንብረትና በአካባቢው ካሉት የንግድ ባንክና ሌሎች ድርጅቶች መትረፍ አንፃር በእሳቱ የወደመው ንብረት ትንሽ መሆኑን አቶ ንጋቱ አክለዋል፡፡

 

በሽብርተኝነት ተጠርጥረው የተከሰሱ ሙስሊሞች የመከላከያ ምስክሮቻቸውን ሳያሰሙ ቀሩ

$
0
0

-477 የመከላከያ ምስክሮችን ቆጥረዋል

በሃይማኖት ሽፋን የፖለቲካ ግብ አስቀምጠው የተለያዩ የሽብር ተግባራትን ለመፈጸም ሲንቀሳቀሱ ተደርሶባቸዋል በሚል ተጠርጥረው ከታሰሩና ክስ ከተመሠረተባቸው ሙስሊሞች መካከል፣ አሥራ ዘጠኙ የመከላከያ ምስክሮቻቸውን ማሰማት የሚጀምሩት ጥር 26 ቀን 2006 ዓ.ም. የነበረ ቢሆንም ሳያሰሙ ቀሩ፡፡

በኢትዮጵያ ሃይማኖታዊ መንግሥት የመመሥረት ዓላማ አላቸው በሚል የተከሰሱት ተጠርጣሪዎች፣ 477 ምስክሮቻቸውን ለማሰማት አቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ውስጥ በሚገኘው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አራተኛ ወንጀል ችሎት የተገኙ ቢሆንም፣ እያንዳንዱ የመከላከያ ምስክር በማን ላይ ምን እንደሚያስረዳ ጭብጥ ባለማስያዛቸው የመከላከያ ምስክሮቻቸውን ማሰማት አለመቻላቸው ተገልጿል፡፡ 

የተጠርጣሪዎቹ የመከላከያ ምስክሮች ስለሚያስረዱት የምስክርነት ቃል ለፍርድ ቤቱ ማቅረብ እንዳለባቸው ፍርድ ቤቱ ሲገልጽ፣ ዓቃቤ ሕግም የመከላከያ ምስክሮቹ ቁጥር ብቻ ሳይሆን ዝርዝራቸውም እንዲደርሰው ትዕዛዝ እንዲሰጥለት ለፍርድ ቤቱ አመልክቶ ነበር፡፡ 

የተጠርጣሪዎቹ ጠበቆች የዓቃቤ ሕግን ማመልከቻ በመቃወም ለፍርድ ቤቱ እንደገለጹት፣ ዓቃቤ ሕግ የምስክሮቹን ቁጥር ከመግለጽ ውጪ የአንዳቸውንም ስም ዝርዝር አላስታወቀም፡፡ በወቅቱ ግን እነሱም የዓቃቤ ሕግ ምስክሮች ስም ዝርዝራቸው እንዲሰጣቸው ጠይቀው እንደነበር አስታውሰው፣ የዓቃቤ ሕግ ምላሽ ‹‹ለምስክሮቼ ደኅንነት ስል ስማቸውን መግለጽ አልችልም፤›› የሚል እንደነበር አስረድተዋል፡፡ 

በመሆኑም እነርሱም በደንበኞቻቸው የመከላከያ ምስክሮች ላይ ተፅዕኖ እየደረሰ መሆኑን በመጠቆም፣ ለደኅንነታቸው ስለሚሰጉ ስማቸውን መግለጽ እንደማይፈልጉ ለፍርድ ቤቱ በማሳወቅ የዓቃቤ ሕግን ጥያቄ ተቃውመዋል፡፡

ዓቃቤ ሕግ የተጠርጣሪ ጠበቆች ያነሱት ሥጋት ስህተት መሆኑን በመጠቆምና እውነት ከሆነ እሱም መከታተልና ሁኔታውን ማጣራት እንደሚፈልግ በመግለጽ፣ ማን የትና በማን ላይ የማሰፈራራትም ሆነ ሌላ ተፅዕኖ ያደረሰ ካለ ተጠርጣሪዎች ወይም ጠበቆቻቸው ግልጽ እንዲያደርጉ ችሎቱን ጠይቋል፡፡

ፍርድ ቤቱ የተጠርጣሪ ጠበቆች ምላሽ እንዲሰጡ ሲጠይቃቸው፣ የመከላከያ ምስክሮቻቸው ማን በማን ላይ ምን እንደሚያስረዳ ለማቅረብ የአንድ ወር ጊዜ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል፡፡ ፍርድ ቤቱም ጥያቄያቸውን በመቀበል ለመጋቢት 16 ቀን 2006 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀጠሮ በመስጠት ለተከታታይ 15 ቀናት የመከላከያ ምስክሮችን ቃል እንደሚሰማ አስታውቋል፡፡  

 

የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ የሀብት ቁጥጥር ሥርዓት አለማስፈኑን አመነ

$
0
0

በኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የሀብት ቁጥጥርና ክትትል ሥርዓት አለመስፈኑንና የቦርዱ ጽሕፈት ቤት አወቃቀር ሲበዛ ኋላቀር መሆኑን፣ የጽሕፈት ቤቱ ኃላፊዎች ለፓርላማው በሰጡት ምላሽ አመኑ፡፡ 

የጽሕፈት ቤቱ ኃላፊዎች ባለፈው ሳምንት በፓርላማው የመንግሥት ወጪ አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ፊት ቀርበው፣ መወራረድ ስላልቻሉ በርካታ ሚሊዮን ብሮች ባስረዱበት ወቅት ነው የጽሕፈት ቤቱን ችግሮች በግልጽ ለማመን የተገደዱት፡፡ 

የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሥርያ ቤት በ2004 ዓ.ም. በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ላይ ባደረገው ኦዲት፣ በሚሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብ መወራረድ አለመቻሉን ለፓርላማው በግንቦት ወር 2005 ዓ.ም. ሪፖርት አድርጐ ነበር፡፡ 

ከእነዚህ መካከል በዋነኝነት የሚጠቀሰው ከ1995 እስከ 2004 በጀት ዓመት ድረስ ለምርጫ ማስፈጸሚያ በሰነድ ተሰጥቶ ሳይሰበሰብ የቀረ 15.9 ሚሊዮን ብር መኖሩን ሪፖርቱ ይገልጻል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ለሦስት የፖለቲካ ፓርቲዎች የተከፈለ 1.9 ሚሊዮን ብር መኖሩ ቢገለጽም፣ ፓርቲዎቹ ገንዘቡን ስለመቀበላቸው ማስረጃ አለመኖሩን፣ ገንዘቡ የገባበት የባንክ ቁጥር የፓርቲዎቹ ስለመሆኑ ማረጋጋጫ ሳይቀርብ በወጪ ተመዝግቦ መገኘቱ፣ እንዲሁም 1.57 ሚሊዮን ብር በጉድለት መታየቱ በዋና ኦዲተሩ ሪፖርት ከተጠቀሱት መካከል ይገኙበታል፡፡ 

ይህንን የኦዲት ሪፖርት በማስመልከት የፓርላማው ቋሚ ኮሚቴ የቦርዱን አመራሮችና የጽሕፈት ቤቱን ኃላፊዎች በመጥራት የኦዲት ግኝቱን በተመለከተ ምን እንዳደረጉ ጥያቄ አቅርቦላቸዋል፡፡ 

የጽሕፈት ቤቱ ዋና ጸሐፊ አቶ ነጋ ዱፌሳ፣ የጽሕፈት ቤቱ ምክትል ኃላፊ አቶ ወንድሙ ጐላና የቦርዱ ምክትል ሰብሳቢ ዶ/ር አዲሱ ገብረ እግዚአብሔር ፓርላማ ተገኝተው ጉድለቶችን ለማስተካከልና ያልተወራረዱ ሒሳቦችን ለማወራረድ ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ 

ከተጠቀሰው 15.9 ሚሊዮን ብር ተሰብሳቢ ሒሳብ ውስጥ በአሁኑ ወቅት 7.1 ሚሊዮን ብር የሚሆነውን ማወራረዳቸውን የገለጹት ኃላፊዎቹ፣ እስካሁን ማወራረድ ካልተቻለባቸው ምክንያች መካከል ከትምህርት ተቋማትና ከመከላከያ ሠራዊት ተቋማት በምርጫ ማስፈጸም ላይ ተሰማርተው የነበሩ ሠራተኞች በተቋማቱ ባህሪ የተነሳ ሊገኙ ባለመቻላቸው ነው ብለዋል፡፡ 

በጉድለት ለተገኘው 1.57 ሚሊዮን ብር ተጠያቂ በሆኑ ግለሰቦች ላይም ክስ ተመሥርቶ ሁለቱ በሕግ ቁጥጥር ሥር ውለው ጉዳያቸውን እየተከታተሉ ነው ብለው፣ በተጨማሪም ለሦስት ፓርቲዎች ስለተለቀቀው ገንዘብ ማረጋገጫ በአሁኑ ወቅት ሦስቱም ፓርቲዎች ማስረጃ ማቅረባቸውን አስረድተዋል፡፡   

የቋሚ ኮሚቴው አባላት እየተደረገ ያለውን ጥረት በተወሰነ ሁኔታ የተቀበሉት ቢሆንም፣ ለተቋሙ የሀብት ብክነት መነሻ በሆኑ ጉዳዮች ላይ ሥርዓት መዘርጋት ካልተቻለ ችግሮቹን በዘላቂነት መፍታት እንደማይቻል አሳስበዋል፡፡ 

ዋና ኦዲተር ለፓርላማው ሪፖርት ባቀረበባቸው ጊዜያት የምርጫ ቦርድ ስም በችግር ሳይነሳ ቀርቶ እንደማያውቅ የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ አቶ ተሾመ እሸቱ ገልጸዋል፡፡ 

‹‹እንደ ግለሰብ እንደዚህ ዓይነት ስም ሊኖረኝ አልፈልግም፡፡ ወይ ትቼው እሄዳለሁ ወይ ተቋሙን እቀይረዋለሁ፡፡ ይህንን የምንላችሁ ዝም ብለን አይደለም፡፡ ተቋሙ ካለው ልዩ ባህሪ ነው፡፡ በውሸትም በእውነትም የሚቀጠሉ ስሞች ሊሰጠው ይችላል፡፡ ይህንን ተጋላጭነት መቀነስ የግድ ነው፤›› ሲሉ አቶ ተሾመ አሳስበዋል፡፡ 

የጽሕፈት ቤቱ ምክትል ኃላፊ አቶ ወንድሙ በሰጡት ምላሽ፣ ‹‹የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ጽሕፈት ቤት ሲበዛ ኋላቀር ነው፡፡ በጭራሽ የሲቪል ሰርቪስ ሪፎርም አይቶት አያውቅም፤›› ብለዋል፡፡ 

በ2004 ዓ.ም. ችግሮቹን ለመለየት ቢሞከርም የሥራ ሒደት ለውጥ ፕሮግራሙን ተግባራዊ ማድረግ አለመቻሉን የገለጹት አቶ ወንድሙ፣ ‹‹የለውጥ ሥራውን መተግበር ጀምረን ችግሩ ከቀጠለ ክቡር ሰብሳቢው እንዳሉት እኛ መኖር የለብንም፤›› ሲሉ ችግሩን አስረድተዋል፡፡     

 

ግብፅ ሱዳንን ከኢትዮጵያ ለመነጠል ዲፕሎማሲያዊ ዘመቻ ጀመረች

$
0
0
ግብፅ ሱዳንን ከኢትዮጵያ ለመነጠል ዲፕሎማሲያዊ ዘመቻ ጀመረች

-የግብፅ የልዑካን ቡድን በህዳሴው ግድብ ላይ ከአፍሪካ ኅብረት ጋር ሊነጋገር ነው

የግብፅ መንግሥት በታላቁ የህዳሴ የኃይል ማመንጫ ግድብ በተመለከተ ሱዳን ለኢትዮጵያ የሰጠችውን ድጋፍ ለማጨናገፍ፣ ሱዳንን ከኢትዮጵያ ለመነጠል ዲፕሎማሲያዊ ዘመቻ መጀመርዋን ዘገባዎች አመለከቱ፡፡

የተለያዩ የግብፅ መገናኛ ብዙኃን ሰሞኑን እንደዘገቡት፣ የግብፅ መንግሥት የተለያዩ የመንግሥት አመራሮችና ፖለቲከኞች ከሱዳን መንግሥት አቻዎቻቸው ጋር ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ጀምረዋል፡፡

ለአብነት ከተጠቀሱት መካከል የግብፅ አል ዋፍድ ፓርቲ ሊቀመንበር ሳይድ አል ባዳዊ በካይሮ ከሱዳን አምባሳደር ከማል ሐሰን ዓሊ ጋር በሁለቱ አገሮች ድንበር የፀጥታ ጉዳዮች ላይ በዋነኝነት መክረዋል፡፡ በሁለቱ አገሮች ድንበር የጦር መሣሪያ ዝውውር ለማስቆም የተነጋገሩት ሁለቱ ባለሥልጣናት፣ ኢትዮጵያ እየገነባችው ባለው የታላቁ ህዳሴ የኃይል ማመንጫ ግድብና በሱዳን አቋም ላይ ተነጋግረዋል፡፡

ከውይይታቸው በኋላ አል ባዳዊ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ሱዳን በታላቁ የህዳሴ ግድብ ላይ ያላት አቋም ከኢትዮጵያ ጋር ተመሳሳይ ነው መባሉ በእውነት ላይ ያልተመሠረተ ተባራሪ ወሬ ነው ብለዋል፡፡ 

በግድቡ ላይ ሦስቱ አገሮች ጥልቅ ውይይት አካሂደው የሁሉንም ወገን ጥያቄዎች በሚመለስ ደረጃ መግባባት ይኖርባቸዋል የሚሉት አል ባዳዊ፣ ሱዳን የግብፅን የውኃ ፍላጐት በሚነካና ብሔራዊ ደኅንነቷን በሚጐዳ ጉዳይ ላይ አሉታዊ አቋም አትይዝም ሲሉ አስታውቀዋል፡፡ 

የሱዳን የመገናኛ ብዙኃን ባለፈው ሰኞ ዘገባዎቻቸው የሱዳን የመከላከያ ሚኒስትር በዚህ ሳምንት ወደ ካይሮ በማቅናት ከግብፅ አቻቸው ከፊልድ ማርሻል አብዱልፋታህ አል ሲሲ ጋር በሁለቱ አገሮች የጋራ የደኅንነት ጉዳዮች ላይ ይመክራሉ ተብሎ ይጠበቃል ብለዋል፡፡ በተመሳሳይ የሱዳን የመስኖ ሚኒስትር ወደ ግብፅ በዚህ ሳምንት እንደሚያመሩ የሱዳን ትሪቡን ዘገባ ያመለክታል፡፡ 

የግብፅ የመስኖ ሚኒስትር መሐመድ አብዱል ሙታሊብ ባለፈው ሰኞ በሰጡት መግለጫ ደግሞ ኢትዮጵያ የህዳሴውን ግድብ ግንባታ ማቆም እንደሚገባት ተናግረዋል፡፡ ‹‹ኢትዮጵያ በዓባይ ላይ የኃይል ማመንጫ ግድብ መገንባት ከፈለገች መጠኑ አነስተኛ መሆን ይገባዋል፤›› ብለዋል፡፡ እንደሳቸው አባባል የህዳሴው ግድብ ግንባታ ከታቀደው ስድስት ሺሕ ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል የማመንጨት አቅም ወደ 30 በመቶ ዝቅ ማለት አለበት፡፡ በዚህ ስሌት የታላቁ የህዳሴ ግድብ ኤሌክትሪክ የማመንጨት አቅም ወደ 1,800 ሜጋ ዋት መውረድ አለበት፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ 45 አባላትን የያዘ የግብፅ የዲፕሎማሲ ቡድን ከጥር 28 ቀን 2006 ዓ.ም. ጀምሮ ለአምስት ቀናት በኢትዮጵያ ጉብኝት ያደርጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ግብፅ በኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ ላይ ያላትን ተቃውሞ ለአፍሪካ ኅብረት እንደሚያሳውቅና የኢትዮጵያ መንግሥት ባለሥልጣናትንም እንደሚያነጋግር ለመረዳት ተችሏል፡፡

ኢትዮጵያን የሚጐበኘው የልዑካን ቡድን በግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የዲፕሎማሲ ኢንስቲትዩት ኃላፊ አምባሳደር ዓሊ ኣል ሃዲዴ የሚመራ መሆኑን በኢትዮጵያ የግብፅ ኤምባሲ መረጃ ያመለክታል፡፡ የልዑካን ቡድኑ ከአፍሪካ ኅብረት የሰላምና ፀጥታ ምክር ቤት ኃላፊና ከኅብረቱ የመሠረተ ልማትና ኢነርጂ ኮሚሽነር ጋር እንደሚመክር የተያዘው ፕሮግራም ያስረዳል፡፡ 

በተጨማሪም ከኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት፣ ከዓባይ ተፋሰስ ዳይሬክቶሬትና ከሕግ ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ኃላፊዎች ጋር እንደሚነጋገር ታውቋል፡፡ እንዲሁም ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትሪያርክና ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን ጋር በመገናኘት በህዳሴው ግድብ ላይ ይመክራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

በቅርቡ ሪፖርተር ያነጋገራቸው የውኃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስቴር የወሰንና ወሰን ተሻጋሪ ወንዞች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ፈቅአህመድ ነጋሽ፣ ሱዳን በህዳሴው ግድብ ላይ ከኢትዮጵያ ጋር የወገነችው ለራሷ ኢኮኖሚያዊ ጥቅም እንደሆነ አብራርተዋል፡፡ በአጋጣሚ ለድርድር በካርቱም በቆዩባቸው ጊዜያት በተለያዩ መስጊዶች ውስጥ ሳይቀር የኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ ፕሮጀክት ሱዳንን እንዴት ሊጠቅም እንደሚችል ሲሰበክ በግርምት መታዘባቸውን በመግለጽ፣ ሱዳን ከኢትዮጵያ ጐን ለራሷ ጥቅም ስትል መቆሟን መረዳት ይቻላል ብለዋል፡፡

የግብፅ ባለሥልጣናት ከኢትዮጵያ ጋር በሚደረገው ውይይትም ሆነ ድርድር ሱዳን የግብፅን ጥቅም የሚፃረር አቋም እንድትይዝ አለመፈለጋቸው ቢነገርም፣ ሱዳን እስካሁን የግድቡን ግንባታ እንደምትደግፍ ነው የሚታወቀው፡፡ ሱዳን ከኢትዮጵያ ጎን ለመሰለፍ የቻለችው በሦስቱ አገሮች ተወክሎ ሲሠራ የነበረውና ዓለም አቀፍ ባለሙያዎችን ያካተተው የኤክስፐርቶች ፓነል ሪፖርት ድምዳሜን አገናዝባ ነው፡፡ በሪፖርቱ ግድቡ በሱዳንም ሆነ በግብፅ ላይ ይህ ነው የሚባል ጉዳት እንደማያደርስ ማረጋገጡ ይታወሳል፡፡ ምንም እንኳ የግብፅ ባለሥልጣን የሱዳን አቋም ከኢትዮጵያ ጋር ወግኗል መባሉን ተባራሪ ወሬ ነው ቢሉም፣ የሱዳን ባለሥልጣናት በአደባባይ ድጋፋቸውን መግለጻቸው አይዘነጋም፡፡  

 

የአብነት ትምህርት ቤቶች ከዘመናዊ ትምህርት ጋር የሚተዋወቁበት አሠራር ተግባራዊ ሊሆን ነው

$
0
0

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን መዋቅር ውስጥ መሠረታዊ ሚና ያላቸውና የዛሬዎቹ ዘመናዊ የትምህርት ተቋማት ተምሣሌቶች መሆናቸው የሚነገርላቸው የአብነት ትምህርት ቤቶች፣ ከዘመናዊ ትምህርት ጋር ሊተዋወቁ መሆኑን ማኅበረ ቅዱሳን አስታወቀ፡፡ 

የቅኔ፣ የትርጓሜ መጻሕፍትና የአቋቋም ትምህርት ክፍሎችን የሚያካትቱት የአብነት ትምህርት ቤቶች ለቤተ ክርስቲያኒቱ ህልውና ምሰሶ መሆናቸውን የሚገልጹት የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ፀሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢሆነኝ፣ የምዕተ ዓመቱን የልማት ግቦች ተከትሎ አገሪቱ ማንኛውም ዕድሜው ለትምህርት የደረሰ ሕፃን ወደ ትምህርት ቤት እንዲገባ ማስገደዷ ለአብነት ትምህርት ቤቶች ህልውና አደጋ ሊሆን ይችላል፡፡ 

በመሆኑም የአብነት ትምህርት ቤቶች ተመናምነው ቤተ ክርስቲያኒቱም ሆነች አገሪቱ ተጎጂ ከመሆናቸው በፊት ዘመናዊ ትምህርቱን በየደረጃው በአብነት ትምህርት ቤት ውስጥ ማስፋፋት የግድ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት፣ ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዘርፍ ዋና ተጠሪ የሆኑት ወ/ሮ ዓለምፀሐይ መሠረት ዘመናዊ ትምህርት በአብነት ትምህርት ቤቶች ውስጥ የሚሰጥበትን መንገድ አብራርተዋል፡፡ በአሃዳዊ የትምህርት ሥርዓቱ ከአንደኛ እስከ አራተኛ ክፍል ድረስ በዚያው በአብነት ትምህርት ቤቶቹ ውስጥ ሊሰጥ እንደሚችልና ከአምስተኛ ክፍል በላይ ግን ተማሪዎቹ በአቅራቢያቸው ወደሚገኙ ዘመናዊ ትምህርት ቤቶች ሄደው እንደሚማሩ ገልጸዋል፡፡ 

የአብነት ተማሪዎቹ በሁለቱም ትምህርት ቤቶች ውስጥ ለመማር ሲገደዱ ለቀለብና መሰል ጉዳዮች የሚንቀሳቀሱበት ትርፍ ጊዜ ስለማያገኙ፣ ማኅበሩ በኢትዮጵያዊው የቤተ ክህነት ሊቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ስም ነፃ የትምህርት ዕድል እንደሚያዘጋጅላቸውም ተጠቁሟል፡፡ የዘመናዊ ትምህርቱን አሰጣጥ በዋናነት ትምህርት ሚኒስቴር በየወረዳውና ዞኑ በሚገኙት ቢሮዎች በኩል የሚቆጣጠረው ሲሆን፣ የመምህራን ደመወዝና ተያያዥ ወጪዎችን ግን ማኅበሩ ለመሸፈን እንደሚገደድ ተገልጿል፡፡

በተያያዘ ዜናም ማኅበሩ የካቲት 2 ቀን 2006 ዓ.ም. በሚያካሂደው ሦስተኛው የአብነት ትምህርት ቤቶች የሊቃውንት ጉባዔ ይኼው ጉዳይና ሌሎች ቤተ ክርስቲያኒቱን ከአገራዊ አጀንዳዎች ጋር የሚያገናኟትን ጉዳዮች እንደሚመክርባቸው አስታውቋል፡፡ 

 

በአቶ ቃሲም ፊጤ ክስ ላይ ምስክሮችን መስማት ተጀመረ

$
0
0
በአቶ ቃሲም ፊጤ ክስ ላይ ምስክሮችን መስማት ተጀመረ

በሥልጣን ያላግባብ መገልገል የሙስና ወንጀል ተጠርጥረው ክስ የተመሠረተባቸው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የመሬት ልማትና ግንባታ ፈቃድ ባለሥልጣን ሥራ አስኪያጅ አቶ ቃሴም ፌጤና ሦስት የቀድሞ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የተለያዩ ክፍሎች ኃላፊዎች ላይ፣ የፀረ ሙስና ኮሚሽን ዓቃቤ ሕግ ምስክሮችን አቅርቦ ማሰማት ጀመረ፡፡

ክሱን እየመረመረው ለሚገኘው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ አንደኛ ወንጀል ችሎት ጥር 27 ቀን 2006 ዓ.ም. ቀርበው ምስክርነታቸውን የሰጡት፣ የኮሚሽኑ የዓቃቤ ሕግ የመጀመርያው ምስክር ለክሱ መመሥረት ምክንያት የሆኑት ኢንጂነር ግርማ አፈወርቅ የተባሉ ግለሰብ ናቸው፡፡

ኢንጂነር ግርማ ግማሽ ቀን በፈጀው የምስክርነታቸው ቃል የቤት ችግርን ለመቅረፍ ከአዲስ አበባ አስተዳደር ኃላፊዎች ጋር በመሆን የነፃ አገልግሎት መስጠታቸውንና መሐንዲስ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ በሪሰርችና ዴቨሎፕመንት ቴክኖሎጂ ለ35 ዓመት ማገልገላቸውን፣ ከኢሕአዴግ የመጀመርያዎቹ ከንቲባዎች እስከ አቶ ኩማ ደመቅሳ ድረስ ግንኙነት እንደነበራቸውና የራሳቸውን አስተዋጽኦ በነፃ ማበርከታቸውን በተደጋጋሚ ገልጸዋል፡፡

የቤት ችግር በአጭር ጊዜ እንዴት መፍትሔ ሊያገኝ እንደሚችል ከከንቲባ ኩማ ካቢኔ ጋር ሲመካከሩ፣ ኢንጂነር ግርማ መፍትሔ እንዳላቸው ወይም በፓይለት ፕሮጀክት አንድ ፈጣን የቤት መገንባት ሥልት እንደሚያሳዩ ሐሳብ ሲያቀርቡ፣ አስተዳደሩ በመስማማት ከአምስት ሺሕ እስከ አሥር ሺሕ ካሬ ሜትር እንደሚሰጣቸው ሲነግራቸው፣ ‹‹አይሆንም የምፈልገው በራሴ ይዞታ ላይ ቴክኖሎጂውን ማሳየት ነው፤›› በማለታቸው፣ አቶ ኩማ በሥራቸው የሚገኙትን አቶ ኃይሌ ፍሰኃንና አቶ ቃሲም ፊጤን እንዳስተዋወቋቸው ተናግረዋል፡፡

ከአቶ ኃይሌ ጋርም ሆነ ከአቶ ቃሲም ጋር ጥሩ ግንኙነት የነበራቸው ቢሆንም፣ ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ከአቶ ቃሲም ጋር ግንኙነታቸውን ጥሩ እንዳልሆነ የገለጹት እንጂነር ግርማ፣ ምክንያቱም አንድ ዶክተር ሲኤምሲ አካባቢ ለሆስፒታል መገንቢያ በሊዝ የወሰዱትን ቦታ እሳቸው መካከለኛ ገቢ ላላቸው ሰዎች 172 አፓርትመንቶችን ሊገነቡ ካቀረቡት ፕሮፖዛል ጋር በተገናኘ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡

በእነ አቶ ቃሲም ላይ በዋናነት ስለቀረበው ክስ እንዲያስረዱ ተጠይቀው፣ መንግሥት በቦሌ ከፍለ ከተማ  በቀድሞው ከፍተኛ 17 ቀበሌ 19 ውስጥ 500 ካሬ ሜትር ቦታ በ1987 ዓ.ም. የተሰጣቸው ቢሆንም፣ ከቀበሌ እስከ አስተዳደሩ ያሉ ኃላፊዎች ሊያስረክቡዋቸው ባለመቻላቸው በከተማ ነክ ፍርድ ቤት ክስ መሥርተው በ2002 ዓ.ም. መረከባቸውን አስረድተዋል፡፡ ቦታው በጂአይኤስ 470 ካሬ ሜትር እንደሆነ ቢነገራቸውም፣ በባለሙያ አስጠንተው 500 ካሬ ሜትር መሆኑን ማረጋጋጣቸውን ጠቁመዋል፡፡

ለሚገነቡት ባለ 17 ፎቅ ሕንፃ 90 በመቶ የሚሆነው የሕንፃ ክፍል (ስትራክቸር) ከውጪ ለማስመጣት ኤልሲ ከፍተው በመንቀሳቀስ ላይ እያሉ፣ ሲኤምሲ ዶ/ር አብረሃም ለሚባሉ ግለሰብ ለሆስፒታል ግንባታ የተወሰደና ወደሳቸው የዞረው ቦታ ካርታ መሰረዙን መስማታቸውን የገለጹት ኢንጂነር ግርማ፣ ችግሩን ለማስተካከል እላይ እታች ሲሉ ነገሮች ሁሉ መቀያየራቸውን ገልጸዋል፡፡

በክሱ ከተካተቱት የአስተዳደሩ የመሬት አቅርቦት አፈጻጸም የንዑስ የሥራ ሒደት ከአቶ በቀለ ገብሬ በስተቀር አቶ ቃሲምም ሆኑ ሌሎቹ ኃላፊዎች ቀና ምላሽ እንደነፈጓቸው የገለጹት ኢንጂነሩ፣ ቦሌ ያለው 500 ካሬ ሜትር ቦታ ካርታው ተሰርዞ ለሌላ መሰጠቱን፣ በቦታው ላይ ሠርተውት የነበረው የጥበቃ ቤት ፈርሶ በሕገወጥ መንገድ ቦታውን መነጠቃቸውን አብራርተዋል፡፡ አስተዳደራዊ በደል እንደደረሰባቸው ለአቶ ኩማ ቢያመለከቱም ምላሽ ሊያገኙ ባለመቻላቸው፣ ለከንቲባው ያስገቡትን ማመልከቻ ለፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ማቅረባቸውን ገልጸዋል፡፡

ሁለተኛው የዓቃቤ ሕግ ምስክር ያስረዱት ኢንጂነር ግርማ በአዲስ አበባ ከተማ ነክ ፍርድ ቤት  የተወሰነላቸውን ውሳኔ ተከትሎ፣ የአስተዳደሩ ምርመራና ክስ ኤክስፐርት ለቀድሞው ሊዝ ቦርድ በሰጡት አስተያየት ላይ ያተኮረ ነበር፡፡ ፍርድ ቤቱ ኢንጂነሩ ሕጋዊ ባለይዞታ መሆናቸውን ያረጋገጠ ቢሆንም፣ ኤክስፐርቱ የከተማ ነክ መጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት ውሳኔ በሰበር ችሎት እንደተሰረዘና ባለይዞታነታቸው የተሻረ በማስመሰል አስታያየት መሰጠቱን በሚመለከት ለፍርድ ቤቱ አስረድተዋል፡፡ አንድ ግለሰብ የሆቴል ማስፋፊያ ጥያቄ ማቅረባቸውን ተከትሎ ሰነዶች ሲመረመሩ፣ 500 ካሬ ሜትር ቦታው ለኢንጂነር ግርማ መሰጠቱን የሚያመለክት የፍርድ ቤት ውሳኔ መገኘቱን፣ ነገር ግን ሌሎች ሦስት ግለሰቦች ይዞታው የእነሱ መሆኑን በመጥቀስ ለከተማ ነክ ፍርድ ቤት ሲከሱ፣ ፍርድ ቤቱ ውድቅ ስላደረገባቸው ጉዳዩን ወደ ሰበር ችሎት ሲወስዱት፣ ሰበር ችሎቱ የሥር ፍርድ ቤት ውድቅ ሊያደርግባቸው እንደማይገባ በመግለጽ መዝገቡን ዘግቶ ሲያሰናብታቸው፣ ኢንጂነር ግርማ በፍርድ ቤት ያገኙት መብት እንደተሰረዘ በማድረግ የሕግ ኤክስፐርቱ አስተያየት መስጠታቸውን መስክረዋል፡፡ 

በተለይ በሁለተኛው ምስክር ላይ ከተከሳሾች በርካታ የመስቀለኛ ጥያቄዎች የቀረበላቸው ቢሆንም፣ የሥራ ሰዓት በመጠናቀቁ መዝገቡ በይደር ለየካቲት 12 ቀን 2006 ዓ.ም. ተቀጥሯል፡፡

 

ሕብር ስኳር ከሦስት ወራት ንትርክ በኋላ በአዲስ ቦርድ ሥራውን ጀመረ

$
0
0
ሕብር ስኳር ከሦስት ወራት ንትርክ በኋላ በአዲስ ቦርድ ሥራውን ጀመረ

ሕብር ስኳር ከሦስት ወራት ንትርክ በኋላ አዲስ ቦርድ ሰይሞ ሥራውን መጀመሩን አስታወቀ፡፡ በዚህም መሠረት በሁለት ሺሕ ሔክታር መሬት ላይ ምንጣሮ ለመጀመር መነሳቱን ገልጿል፡፡ 

ጥቅምት 24 ቀን 2006 ዓ.ም. በተካሄደው ጉባዔ የሕብር ስኳር አክሲዮን ማኅበር የቦርድ አመራር አባላትን ለመምረጥ ከቀረቡት 19 ዕጩዎች መካከል ሁለቱ የአክሲዮን ማኅበሩ አባል ያልሆኑ ሰዎችን፣ በስህተት እንዲመረጡ በመደረጉ ምክንያት፣ ላለፉት ሦስት ወራት ሥራውን መጀመር ተስኖት መቆየቱ ተገልጿል፡፡

የሕብር ስኳር አክሲዮን ኩባንያን የዳይሬክተሮች ቦርድ አባልና ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ምናላቸው ስማቸው እንዳስታወቁት፣ ኅዳር 14 ቀን 2006 ዓ.ም. ይፋ በተደረገው ውጤት መሠረት በዕጩነት ከቀረቡት መካከል ሁለት ግለሰቦች ሕጋዊ አባል አለመሆናቸው በሰነድና በዳታቤዝ ተረጋግጧል፡፡ አስመራጭ የነበረው ኮሚቴም ለዕጩነት ግለሰቦቹን መልምሎ ሲያቀርብ ስህተት መሥራቱ በመረጋገጡ፣ በዚህ መነሻነት በተፈጠረ አለመግባባት ከሦስት ወራት በላይ ሲጓተት መቆየቱን አስታውቀዋል፡፡ ከ19 ዕጩዎች መካከል ለዳይሬክተሮች ቦርድ 11 አባላት መለየታቸውን አስረድተዋል፡፡ 

የተፈጠረውን ስህተት የደረሰበት የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ ጽሕፈት ቤት ሁለቱን ግለሰቦች ማለትም አቶ አስናቀ ደምሴና አቶ ሞገስ ኃይለ ሥላሴን የኩባንያው ባለአክሲዮኖች አለመሆናቸውን ጠቅሶ፣ በቦርድ አባልነት እንደማይቀበላቸው በማስታወቁ መሆኑን አቶ ምናላቸው ገልጸዋል፡፡ ይህንን የተረዳው የምርጫ አስፈጻሚ ኮሚቴ በተለይ አቶ አስናቀ ደምሴ የተባሉት ግለሰብ፣ የአዲስ አበባ እግር ኳስ አሠልጣኞች ማኅበር ተወካይ ስለሆኑ፣ ይኼው ማኅበርም የሕብር ስኳር አክሲዮን ማኅበር ባለድርሻ ስለሆነ በአቶ አስናቀ ምትክ የአዲስ አበባ እግር ኳስ አሠልጣኞች ማኅበር ገብቶ በቦርድ አባልነት እንዲሠራ አስመራጭ ኮሚቴው ጥያቄ አቅርቦ እንደነበር ተናግረዋል፡፡ 

ይኼንን ጥያቄ ያልተቀበለው የሕብር ስኳር ቦርድ አመራር፣ ባለድርሻው የአዲስ አበባ እግር ኳስ አሠልጣኞች ማኅበር ለቦርድ አባልነት አለመወዳደሩን በመጥቀስ የይተካልኝ ጥያቄውን ውድቅ አድርጎታል ብለዋል፡፡ ኩባንያው ጥያቄውን ውድቅ በማድረጉ ሳቢያም አስመራጭ ከነበሩት መካከል አንዱ ግለሰብ ተቃውሞ በማቅረባቸው ስምምነት ባለመኖሩ የተነሳ ሒደቱ ሲጓተት ቆይቷል በማለት አስረድተዋል፡፡ 

ሕብር ስኳር ለፍትሕ ሚኒስቴርና ለተወካዮች ምክር ቤት ስለተፈጠረው አለመግባባት በማሳወቁ፣ መንግሥት የስድስት ሺሕ ባለአክሲዮኖች ጥቅም በአንድ ግለሰብ አግባብ ያልሆነ አካሄድ ምክንያት መጎዳት የለበትም የሚል ውሳኔ በማሳለፍ ሁለቱ በስህተት የተመረጡት የቦርድ አባላት እስኪተኩ ድረስ፣ በዘጠኝ የቦርድ አባላት ሥራው እንዲቀጥል በሕግ ትዕዛዝ በመሰጠቱ፣ ከጥር 9 ቀን 2006 ዓ.ም. ጀምሮ ይፋዊ እንቅስቃሴ መጀመሩን አቶ ምናላቸው አስታውቀዋል፡፡ 

በዚህም መሠረት የ352 ሚሊዮን ብር በጀት በማፅደቅ፣ በየካቲት ወር 2004 ዓ.ም. ከአማራ ክልል ከተረከበው መሬት ውስጥ በሁለት ሺሕ ሔክታር ላይ ምንጣሮ ለመጀመር ዝግጅት ማደረጉ ተገልጿል፡፡ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ለሕብር ስኳር የብድር አቅርቦት እንደሚሰጥ ይሁንታውን በማሳየቱ፣ የ30 ከመቶ ድርሻ አሟልቶ ብድር ለመጠየቅ ማቀዱንም አክሲዮን ማኅበሩ አስታውቋል፡፡ 

ሕብር ስኳር አክሲዮን ማኅበር ከብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ጋር የፋብሪካ ግንባታ የመግባቢያ ስምምነት ማድረጉ የሚታወስ ሲሆን፣ ለስኳር ኮርፖሬሽን አገዳ ምርት ለማቅረብም እንዲሁ ስምምነት ማድረጉ የሚታወስ ነው፡፡ 

 

 

 


አቶ መላኩና አቶ ገብረዋህድ የተመሠረተባቸውን ክስ ለመቃወም ተጨማሪ ጊዜ ጠየቁ

$
0
0
አቶ መላኩና አቶ ገብረዋህድ የተመሠረተባቸውን ክስ ለመቃወም ተጨማሪ ጊዜ ጠየቁ

-የአቶ ጌቱ ገለቴና ሦስት ግለሰቦች ጉዳይ በሌሉበት እንዲታይ ተወሰነ 

-አቶ መርክነህ ዓለማየሁ ሰነዶች በብሬል ይተርጐሙልኝ አሉ

በከባድ የሙስና ወንጀል ተጠርጥረው ክስ የተመሠረተባቸው የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ዋናና ምክትል ዳይሬክተር የነበሩት አቶ መላኩ ፈንታና አቶ ገብረዋህድ ወልደ ጊዮርጊስን ጨምሮ፣

ከ14 በላይ ተጠርጣሪ ተከሳሾች በቀረበባቸው ክስ ላይ መቃወሚያ ለማቅረብ የተሰጣቸው ጊዜ እንዳልበቃቸው በመግለጽ፣ ተጨማሪ ጊዜ እንዲሰጣቸው ጥር 29 ቀን 2006 ዓ.ም. ፍርድ ቤቱን ጠየቁ፡፡

የኬኬ ድርጅት ባለቤት አቶ ከተማ ከበደንና የነፃና የባሰፋ ትሬዲንግ ባለቤት አቶ ነጋ ገብረ እግዚአብሔርን ጨምሮ በርካቶቹ ተጠርጣሪ ተከሳሾች ለክስ መቃወሚያቸው ከሁለት እስከ 30 ገጾች የሚደርሱ ጽሑፎች በማዘጋጀት ለፍርድ ቤቱና ለዓቃቤ ሕግ ሰጥተዋል፡፡ 

ፍርድ ቤቱ መዝገቡን ቀጥሮ የነበረው ተጠርጣሪ ተከሳሾች መቃወሚያቸውን እንዲያቀርቡና በተደጋጋሚ ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ ቢያዝም ሊቀርቡ ያልቻሉት አቶ ጌቱ ገለቴ፣ አቶ ገዳ በሽር፣ አቶ ታደሰ ፈይሳና አቶ ነጋ ቴኒ በጋዜጣ ተጠርተው እንዲቀርቡ በሚል ያዘዘውን ለመጠባበቅ ነበር፡፡ በትዕዛዙ መሠረት ሁሉም ተጠርጣሪዎች የክስ መቃወሚያቸውን ማቅረብ ባይችሉም የተወሰኑት አቅርበዋል፡፡ በጋዜጣ እንዲጠሩ የተባሉት ግን በአዲስ ዘመን ጋዜጣ ጥር 23 ቀን 2006 ዓ.ም. ዕትም መጠራታቸው ተገልጿል፡፡ በመሆኑም አራቱም ተጠርጣሪ ተከሳሾች ሊቀርቡ አለመቻላቸው መረጋገጡን በመጠቆም፣ የተጠረጠሩበት ክስ በሌሉበት እንዲታይ ውሳኔ ማሳለፉን ፍርድ ቤቱ ገልጿል፡፡ 

ከተጠርጣሪ ተከሳሾች መካከል የገቢዎችና ጉምሩክ ምክትል ዋና ዓቃቤ ሕግ የነበሩት አቶ መርክነህ ዓለማየሁ ለፍርድ ቤቱ አቤቱታ አቅርበዋል፡፡ አቶ መርክነህ የአካል ጉዳተኛ (ዓይነ ስውር) መሆናቸውን በመግለጽ፣ ክርክሩ ሰፊ ስለሆነ በመስማት ብቻ የክሱን ጭብጥ ለመያዝ እንደሚያስቸግራቸው ተናግረዋል፡፡ ጸሐፊም ሆነ አንባቢ እንደሌላቸው ጠቁመዋል፡፡ 

በመሆኑም በክርክሩ ወቅት ፍትሐዊ ተሳትፎ ለማድረግ እንደማይችሉ በመጠቆም፣ የክስ ማስረጃ ሰነዶች በሙሉ በብሬል ተተርጉመውና ተዘጋጅተው እንዲደርሱዋቸው ለከሳሽ ዓቃቤ ሕግ ትዕዛዝ እንዲሰጥላቸው አመልክተዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ በተለይ የአቶ መርክነህ ጥያቄ የመብት ጥያቄ መሆኑን በመግለጽ፣ ማመልከቻቸውን በጽሑፍ አድርገው በጽሕፈት ቤት በኩል እንዲያቀርቡ በመንገር፣ የክስ መቃወሚያ ያላቀረቡ ተጠርጣሪ ተከሳሾች መቃወሚያቸውን የካቲት 10 ቀን 2006 ዓ.ም. እንዲያቀርቡ  በማዘዝ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

 

 

መንግሥት ለአበባና ለፍራፍሬ ምርት መሬት ለማስገኘት ከክልሎች ጋር ውይይት ጀመረ

$
0
0

መንግሥት በዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅዱ ተስፋ የጣለበት የአበባና የፍራፍሬ ኢንቨስትመንት ላለፉት ዓመታት ያሳየው ዝቅተኛ አፈጻጸም በመሬት ችግር ምክንያት በመሆኑ፣ የፌዴራል መንግሥት ከክልሎች ጋር ውይይት ጀመረ፡፡ 

የፌዴራል መንግሥት ውይይቱን እየካሄደ የሚገኘው በተለይ ከኦሮሚያ ክልል ጋር መሆኑን ምንጮች ተናግረዋል፡፡ መንግሥት በአምስት ዓመቱ የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ተስፋ ከጣለባቸው የግብርና ምርቶች መካከል የአበባ፣ የአትክልትና ፍራፍሬ ዘርፍ አንዱ ነው፡፡ ከዚህ ዘርፍ በዕቅድ ዓመቱ መጨረሻ ማለትም በ2007 ዓ.ም. 1.4 ቢሊዮን ዶላር ይጠብቃል፡፡ ይሁን እንጂ በተለያዩ ማነቆዎች የተነሳ መንግሥት ያቀደውን ማግኘት ተስኖታል፡፡ 

ለአብነት ያህል የ2006 የስድስት ወራት የሥራ አፈጻጸም እንኳን ቢታይ ከዕቅዱ በታች መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር መረጃዎች ያስረዳሉ፡፡

የአበባና፣ አትክልትና ፍራፍሬ (ሆርቲካልቸር) ምርት ኤክስፖርት በ2006 ግማሽ ዓመት ውስጥ 202.15 ሚሊዮን ዶላር እንዲያስገኝ ቢታቀድም፣ የተገኘው ግን 106.15 ሚሊዮን ዶላር ማለትም 52.5 በመቶ ብቻ ነው፡፡ በዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዘመኑ ማጠናቀቂያ ማለትም በ2007 ዓ.ም. መጨረሻ 1.4 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ከዘርፉ ለማግኘት ዕቅድ ተይዟል፡፡ 

ይህ ግብ የተጣለው በዕቅዱ መነሻ ዘመን በ2002 ዓ.ም. ከዘርፉ የተገኘውን 201.7 ሚሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሪ መነሻ በማድረግ መሆኑን ከመረጃዎች መረዳት ይቻላል፡፡ ይሁን እንጂ የአምስት ዓመቱ የዕቅድ ዘመን ሊጠናቀቅ የአንድ ዓመት ከግማሽ ብቻ በቀረበት በ2006 ዓ.ም. አጋማሽ ላይ፣ ከዘርፉ ለማግኘት የታቀደው የውጭ ምንዛሪ 202.15 ሚሊዮን ዳላር መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር የስድስት ወራት የዕቅድ አፈጻጸም ያስረዳል፡፡

በግማሽ ዓመት ከዘርፉ ለማግኘት የታቀደው ገቢ ከዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅዱ መነሻ ዓመት ማለትም በ2002 ዓ.ም. ከተገኘው ገቢ ጋር እኩል መሆኑ ጥያቄን ሲያስነሳ፣ በግማሽ ዓመቱ የተገኘው 106.15 ሚሊዮን ዶላር መሆኑ ዘርፉ ከፍተኛ ችግር ውስጥ መውደቁን ለመረዳት ያስችላል፡፡ የግብርና ሚኒስቴር የስድስት ወራት የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ዘርፉ በርካታ ማነቆዎች እንደገጠሙት ይገልጻል፡፡ 

ከእነዚህም መካከል ዋናዎቹ ለነባር አልሚዎች ማስፋፊያና ለአዳዲስ አልሚዎች የሚሆን መሬት በሚፈለገው ፍጥነትና መጠን ማዘጋጀት አለመቻል፣ የሎጂስቲክስና የመሠረተ ልማት በተዘረጋላቸው የክልል ክላስተሮች ለዘርፉ ልማት ተጨማሪ መሬት ለይቶና ተገቢ መሠረተ ልማት በማሟላት ነፃ አድርጐ የማዘጋጀት ሥራ በፍጥነት ማጠናቀቅ አለመቻል መሆናቸውን ይገለጻል፡፡

ጉዳዩን በተመለከተ ከሪፖርተር ጥያቄ የቀረበላቸው የኢትዮጵያ ሆርቲካልቸር ልማት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ዓለም ወልደ ገሪማ፣ ከችግሮቹ መካከል የመሬት አቅርቦት አንዱ መሆኑን ጠቅሰው ችግሩን ለመቅረፍም ከሚመለከታቸው የክልል መንግሥታት ጋር በውይይት ላይ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡

የውይይቱ ይዘት ምን እንደሆነና የመሬት አቅርቦቱን ክልሎቹ በፍጥነት ያላዘጋጁበት ምክንያትን እንዲያብራሩ ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ፣ ውይይቱ ሲጠናቀቅ ዝርዝሩን መናገር እንደሚመርጡ ገልጸዋል፡፡ 

በዕቅድ ዘመኑ ከዘርፉ የሚጠበቀውን ገቢ ለማግኘት አሁን በማምረት ላይ የሚገኙ እርሻዎችን ማስፋፋት፣ በዋናነት ደግሞ አዳዲስ ኢንቨስተሮች ወደ ዘርፉ በስፋት እንዲገቡ ማድረግ የትግበራ አቅጣጫዎች መሆናቸውን ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው የግብርና ሚኒስቴር ኃላፊዎች ይገልጻሉ፡፡ 

እንደ አዲስ ወደ ኢንቨስትመንት መግባት የሚፈልጉ ኩባንያዎች የመሬት ጥያቄ የሚያቀርቡት ከአዲስ አበባ አቅራቢያ በሚገኙ የኦሮሚያ ከተሞች መሆኑን፣ መስፋፋት የሚፈልጉ ነባር እርሻዎችም በዚሁ አካባቢ እንደሚገኙ ኃላፊዎቹ ይናገራሉ፡፡ ይሁን እንጂ የእነዚህን አልሚዎች የመሬት ጥያቄ ለመመለስ ከኦሮሚያ ክልል የመሬት አቅርቦት ማግኘት እንዳልተቻለ ያስረዳሉ፡፡ 

ችግሩን ለመቅረፍም በፌዴራል መንግሥት ደረጃ ከክልሉ መንግሥት ጋር ውይይት መጀመሩን የሚናገሩት እነዚህ ኃላፊዎች፣ የኦሮሚያ ክልል የመሬት አቅርቦቱን በፍጥነት ካልፈታባቸው ምክንያቶች መካከል አንዱ ከሕግ ጉዳዮች ጋር የተገናኘ መሆኑን ይጠቅሳሉ፡፡ የማስፋፊያ ጥያቄው በከተሞች ውስጥ በስፋት የቀረበ በመሆኑና ይህንን ለመመለስ ደግሞ መስተካከል የሚገባቸው የሕግ ማዕቀፎች በመኖራቸው ነው በማለት ያስረዳሉ፡፡ በሆርቲካልቸር ዘርፍ በዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅዱ መጨረሻ ላይ 36,000 ሔክታር መሬት ለማልማት ታቅዷል፡፡

የተጠቀሰውን ሔክታር ለማልማት የተመረጡት ክልሎች በአዲስ አበባ ዙሪያ የኦሮሚያ ልዩ ዞን፣ የሐዋሳና አርባ ምንጭ አካባቢዎች የአዋሽ፣ ድሬዳዋና ሐረር አካባቢዎች፣ የባህር ዳር፣ የዓባይ ሸለቆና የደቡብ ጐንደር አካባቢዎች ናቸው፡፡ ይሁን እንጂ በአጠቃላይ በአገሪቱ በሆርቲካልቸር ዘርፍ እስካለፈው ዓመት የለማው መሬት 12,797 ሔክታር መሆኑን የሆርቲካልቸር ልማት ኤጀንሲ መረጃዎች ያስረዳሉ፡፡  

 

በመንግሥት ላይ ከ16 ሚሊዮን ብር በላይ ጉዳት አድርሰዋል የተባሉ ነጋዴዎች ጥፋተኛ ተባሉ

$
0
0

-ሁለት የኢትዮ ቴሌኮም ኢንጂነሮች ነፃ ወጡ

‹‹ራስ አዲስና ፒሲቶከር›› የተባሉ ሕገወጥ ሶፍትዌሮችንና በሶፍትዌሮቹ ላይ የሚሞሉ የተለያዩ የካርድ ቁጥሮችን ወደ አገር ውስጥ በማስገባትና በማከፋፈል፣ በሕገወጥ መንገድ ስልክ በማስደወል ከ16.6 ሚሊዮን ብር በላይ በመንግሥትና ሕዝብ ላይ ጉዳት አድርሰዋል በሚል ከሦስት ዓመት በፊት ክስ ተመሥርቶባቸው የነበሩ 15 ነጋዴዎች፣ ጥር 28 ቀን 2006 ዓ.ም. ጥፋተኛ ተባሉ፡፡

የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ዓቃቤ ሕግ በመጋቢት ወር 2003 ዓ.ም. በሁለት የኢትዮ ቴሌኮም የሰርቨር አድሚኒስትሬሽንና የኔትወርክ አድሚኒስትሬሽን ኢንጂነሮችና 15 ነጋዴዎች ላይ የመሠረተውን የሙስና ወንጀል ክስ ሲመረምር የከረመው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ ወንጀል ችሎት፣ ሁለቱ ኢንጂነሮች ‹‹ክሳቸውን በሚገባ ተከላክለዋል›› በማለት በነፃ አሰናብቷቸዋል፡፡ 

ነቢያት ጌታሁንና ቢንያም መጋቢ የተባሉ የኢትዮ ቴሌኮም ኢንጂነሮች የተሰጣቸውን የመንግሥት ኃላፊነት ሊከላከሉና ሊጠብቁ ሲገባቸው፣ በሌሉበት ክሳቸው ሲታይ ከነበረው የመዝገቡ ሦስተኛ ተከሳሽ መላኩ ኃይሉ ጎሹ ከሚባሉ ተከሳሽ ጋር በመመሳጠር፣ በሥራ አጋጣሚ ያወቁትን ሚስጥር ጉዳት የሚያደርስ መሆኑን እያወቁ ጥቅም ለማግኘት አሳልፈው መስጠታቸውን ክሱ ያስረዳል፡፡ 

በመሆኑም መላኩ ኃይሉ ጎሹ የሚባሉት ግለሰብ ‹‹ራስ አዲስ እና ፒሲቶከር›› የተባሉ ሕገወጥ ሶፍትዌሮችንና በሶፍትዌሮቹ ላይ የሚሞሉ የካርድ ቁጥሮችን በማስገባት ሲሠሩ ተደርሶባቸው እንዲዘጋ ይደረጋል፡፡ ኢንጂነር ነቢያት ከመላኩ ጋር በመገናኘት እንዲከፍትላቸው ካደረጉ በኋላ ግንኙነታቸው ተጠናክሮ በመቀጠሉና ለሌሎች ሕገወጥ ስልክ አስደዋዮችም ሶፍትዌሮቹን በመስጠት፣ ሕገወጥ ስልክ በማስደወል በመንግሥትና ሕዝብ ጥቅም ላይ ጉዳት ማድረሳቸውን ክሱ ያብራራል፡፡

 የኮሚሽኑ ዓቃቤ ሕግ ክሱን እንዲስረዱለት ያቀረባቸው ምስክሮች አሳማኝ የምስክርነት ቃል በመስጠታቸው ፍርድ ቤቱ  በሰጠው ብይን ሁሉም ተጠርጣሪዎች እንዲከላከሉ ብይን መስጠቱም በመዝገቡ ተገልጿል፡፡ 

ተጠርጣሪ ተከሳሾችም የመከላከያ ምስክሮቻቸውን አቅርበው ያሰሙ ሲሆን፣ ከሁለቱ የኢትዮ ቴሌኮም ኢንጂነሮች በስተቀር ሌሎቹ የዓቃቤ ሕግን ማስረጃና የምስክርነት ቃል ማስተባበል ባለመቻላቸው፣ በዋና ወንጀል አድራጊነት በፈጸሙት የመንግሥት ሥራን በማያመች አኳኋን መምራት የሙስና ወንጀል የ16,624,800 ብር ጉዳት ማድረሳቸው የተረጋገጠ በመሆኑ ጥፋተኛ መሆናቸውን በሰጠው ፍርድ አስታውቋል፡፡ ጥፋተኛ የተባሉት ተከሳሾች የቅጣት ማቅለያ እንዲሁም ከሳሽ ዓቃቤ ሕግ የቅጣት ማክበጃ የካቲት 4 ቀን 2006 ዓ.ም. እንዲያቀርቡ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡

 

 

የአንድነት ፓርቲ አመራር አቶ አሥራት ጣሴ ታሰሩ

$
0
0
የአንድነት ፓርቲ አመራር አቶ አሥራት ጣሴ ታሰሩ

የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) የምክር ቤት አባል አቶ አሥራት ጣሴ ፍርድ ቤት በመድፈር ወንጀል ተከሰው ጥፋተኛ በመባላቸው፣ ጥር 30 ቀን 2006 ዓ.ም. በፖሊስ ጣቢያ ታሰሩ፡፡

አቶ አሥራት ለእስር የበቁበትን ፍርድ ቤት የመድፈር ወንጀል ፈጽመዋል የተባሉት፣ በአዲስ ጉዳይ መጽሔት ቅጽ 7 ቁጥር 198 የጥር ወር 2006 ዓ.ም. ዕትም ላይ በጻፉት ጽሑፍ ምክንያት ነው፡፡

አቶ አሥራት በመጽሔቱ ላይ ባሰፈሩት ‹‹…..አሁን ደግሞ ከሰሞኑ ‘አኬልዳማ’ ድራማ በድጋሚ በተከታታይ እየቀረበ ነው፡፡ ይህ እየሆነ ያለው አንድነት ፓርቲ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ድርጅትን በስም ማጥፋት ወንጀል በፍርድ ቤት ከሶ ገና ውጤት ባልተገኘበት ወቅት ነው፡፡ እሱም ፍትሕ ከኢሕአዴግ ፍርድ ቤቶች ይገኛል ተብሎ ሳይሆን፣ በታሪክ ምስክርነት እንዲመዘገብ ሲባል ነው፤›› በሚለው ዓረፍተ ነገር ፍርድ ቤትን ዘልፈዋል በሚል ጥር 30 ቀን 2006 ዓ.ም. ቀርበው እንዲያስረዱ፣ የፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ዘጠነኛ ፍትሕ ብሔር ችሎት አስጠርቷቸው ነበር፡፡ 

በቀጠሯቸው ቀን ከጠበቃቸው አቶ ተማም አባቡልጉ ጋር የቀረቡት አቶ አሥራት በጠበቃቸው አማካይነት እንደገለጹት፣ ወደ ችሎቱ እንዲቀርቡ ትዕዛዝ የተላለፈበት የሕግ አንቀጽ አግባብነት ያለው ስላልሆነ፣ ክሱ ተሰርዞ በነፃ እንዲሰናበቱ ጠይቀዋል፡፡ ‹‹እሳቸው ተናገሩ ወይም ጻፉ የተባለው ነገር በችሎት ተገኝተው ወይም የክሱ አካል ሆነው ያደረጉት አይደለም፡፡ በችሎትም አልተገኙም፡፡ የክሱ አካልም አይደሉም፤›› ሲሉ ጠበቃው አስረድተዋል፡፡

የተጠቀሰባቸው የሕግ አንቀጽ የሚሠራው በችሎት ተገኝቶ የችሎቱን አሠራር የሚያውክ ወይም ሌላ ተቃራኒ ነገር ላደረገ አካል እንጂ፣ ላልነበረና ፍፁም ግንኙነት ለሌለው አይሆንም በማለት፣ ድርጊቱን የፈጸሙት በሌላ ቦታ ከፍርድ ቤቱ ውጪ በመሆኑ ሊጠሩ እንደማይገባ ጠበቃው አብራርተዋል፡፡ የሕግ ትርጉሙ በጣም ተለጥጦ በማያገባቸውና ሊያስጠራቸው በማይችል ጉዳይ መጠራታቸውን የተቃወሙት ጠበቃው፣ እንዲጠሩበት የተጠቀሰው የሕግ አንቀጽ ከፍርድ ቤት ውጪ ለተከናወነ ድርጊት እንደማይሠራ ጠቁመዋል፡፡ 

ፍርድ ቤቱ፣ ‹‹ከአኬልዳማና ከአንድነት ሌላ ክርክር አላችሁ የላችሁም?›› ብሎ ሲጠይቅ ‹‹የለንም›› ያሉት ጠበቃው፣ አቶ አሥራት በመጽሔቱ ለማብራራት የሞከሩት ከጀሃዳዊ ሐረካት ጋር በተያየዘ ኢሕአዴግ የሚፈራው ሰላምን እንጂ ሽብርተኝነትን አለመሆኑን ለማሳየት እንደሆነ አስረድተዋል፡፡

ዘገባው ስለአጠቃላይ ሁኔታ እንጂ ጉዳዩን ስለሚያየው ችሎት አለመሆኑን፣ የኢሕአዴግ ፍርድ ቤት ሲሉም ኢሕአዴግ መንግሥት ሆኖ በማቋቋሚያ አዋጁ ስላቋቋማቸው ፍርድ ቤቶች እንጂ ስለአንድ ችሎት ነጥለው አለመሆኑን ጠበቃ ተማም አስረድተዋል፡፡

በከሳሽ አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲና በተከሳሽ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ድርጅት መካከል ያለው ክርክር ውጤት ሳይታወቅ፣ ‹‹ከኢሕአዴግ ፍርድ ቤቶች ፍትሕ አይጠበቅም ማለት ምን ማለት ነው?›› በማለት ፍርድ ቤቱ ሲጠይቃቸው፣ አቶ አሥራት የተናገሩት ስለጀሃዳዊ ሥርዓት እንጂ ከአኬልዳማ ጋር የሚገናኝ አለመሆኑን በድጋሚ አቶ ተማም ገልጸዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ መዝገቡን መርምሮ ጥር 30 ቀን 2006 ዓ.ም. ከሰዓት በኋላ በሰጠው ፍርድ ፍርድ ቤቱ የፍትሕ ሥርዓቱን የሚያናጋ ሥራ ተሠርቶ ሲያጋጥመው ወይም ሲሠራ ሲያይ የማስጠራት ሥልጣን አለው ብሏል፡፡ አቶ አሥራት በጻፉት ጹሑፍ የተናገሩት ፍርድ ቤቶችን ጥያቄ ውስጥ የሚጥል መሆኑን፣ ያነሱት አኬልዳማም ሆነ ሌላ ነገር ፍርድ ቤቱ ከያዘው ጉዳይ ውጪ አለመሆኑንና በፍርድ ቤቱ ላይ ጫና የሚያሳድር ዓረፍተ ነገር ተጠቅመዋል ብሏል፡፡ 

በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 29 መሠረት የመናገር፣ የመጻፍና ሐሳባቸውን የመግለጽ መብት ያላቸው ቢሆንም፣ ሌላኛውን ወገን እስካልነኩ ድረስ ብቻ መሆኑን በመጥቀስ አቶ አሥራት ፍርድ ቤትን የመድፈር ወንጀል መፈጸማቸውን በመግለጽ ጥፋተኛ ብሏቸዋል፡፡፡ በመሆኑም አቶ አሥራት እስከ የካቲት 7 ቀን 2006 ዓ.ም. በፖሊስ ጣቢያ እንዲቆዩና የቅጣት ማቅለያ ሐሳባቸውን ይዘው እንዲቀርቡ ትዕዛዝ አስተላልፏል፡፡ የአቶ አሥራት ጣሴ ጠበቃ አቶ ተማም ይግባኝ እንሚጠይቁ አስረድተዋል፡፡

 

‹መፍትሔው አሠልጣኝን ማባረር ሳይሆን ተቋማዊ ለውጥ ማምጣት መቻል ነው››

$
0
0
‹መፍትሔው አሠልጣኝን ማባረር ሳይሆን ተቋማዊ ለውጥ ማምጣት መቻል ነው››

አቶ ሰውነት ቢሻው፣ ተሰናባቹ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ዋና አሠልጣኝ

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ላለፉት ሁለት ዓመታት በላይ በዋና አሠልጣኝነት የመሩት አቶ ሰውነት ቢሻው ሰሞኑን ተሰናብተዋል፡፡

ባለፈው ዓርብ ከሪፖርተር ጋር አጠር ያለ ቃለ ምልልስ ያደረጉት አቶ ሰውነት፣ ከአሠልጣኝነት የተሰናበቱት በፖለቲካ ምክንያት ነው ተብሎ በዓለም አቀፍ ደረጃ የተሰራጨውን ዜና አስተባብለዋል፡፡ ‹‹እኔ የእግር ኳስ አሠልጣኝ እንጂ ፖለቲከኛ አይደለሁም፤›› ያሉት አቶ ሰውነት፣ ‹‹ለምን ተሰናበትኩ የሚል መከራከሪያ የለኝም፤›› ይላሉ፡፡ በቅርቡ በደቡብ አፍሪካ በተካሄደው በቻን ውድድር በተሳተፈውና ውጤት በራቀው ብሔራዊ ቡድን ምክንያት የኢትዮጵያ እግር ኳስ ወድቋል የሚለውን አይቀበሉም፡፡ የውጤት መጥፋት በታላላቅ አገሮችና ቡድኖች ሳይቀር እንደሚያጋጥም አስረድተው፣ እሳቸው ከኃላፊነታቸው ተባረው እግር ኳሱ የተሻለ ደረጃ ላይ የሚደርስ ከሆነ ስንብታቸውን በፀጋ እንደሚቀበሉት አስታውቀዋል፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ ግን መፍትሔው አሠልጣኝ ማባረር ሳይሆን ተቋማዊ ለውጥ ማምጣት መቻል መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ ዝርዝሩን በ ስፖርትገጽ ላይ ይመልከቱ፡፡   

 

ከ45 ሺሕ በላይ ኮንዶሚኒየም ቤቶች ለነዋሪዎች ይተላለፋሉ

$
0
0

-ለተጨማሪ 50 ሺሕ ቤቶች ግንባታ የመሠረት ድንጋይ ይጣላል

በአዲስ አበባ ከተማ ከ45 ሺሕ በላይ ቤቶች በዓመቱ መጨረሻ ለተጠቃሚዎች እንደሚተላለፉ ተገለጸ፡፡ የተገነቡት ቤቶች የሚገኙት በየካ ክፍለ ከተማ የካ አባዶ፣ የካ ጣፎና በቦሌ ክፍለ ከተማ ቦሌ አራብሳ አካባቢዎች ነው፡፡

በየካ አባዶ 15,600፣ በየካ ጣፎ 10,000፣ በቦሌ አራብሳ 20,023 ቤቶች ተገንብተዋል፡፡ በየካ ጣፎ የተገነቡት ቤቶች ዕጣ የወጣባቸው ሲሆኑ፣ በሚቀጥሉት ሁለት ወራት ለተጠቃሚዎቹ ይተላለፋሉ፡፡

በየካ አባዶና በቦሌ አራብሳ የሚገኙት ቤቶች ደግሞ ግንባታቸው እየተካሄደ በመሆኑ እስከ ዓመቱ መጨረሻ ድረስ ለተጠቃሚዎች እንደሚተላለፉ ታውቋል፡፡ 

በየካ አባዶ እየተገነቡ ያሉት ቤቶች የተጀመሩት በጥር 2004 ዓ.ም. ነው፡፡ በዚህ አካባቢ እየተገነቡ ያሉት አነስተኛ ገቢ ላላቸው የኅብረተሰብ ክፍሎች የሚተላለፉት የ10/90 ፕሮግራም ቤቶች፣ መካከለኛ ገቢ ላላቸው የኅብረተሰብ ክፍል የሚተላለፉት የ20/80 ፕሮግራም ቤቶች ናቸው፡፡ 

እነዚህ ቤቶች ከፍታቸው ባለሦስት ወለል፣ ባለአምስት ወለልና ባለስምንት ወለል ሲሆን ባለ ሦስት ወለል ሕንፃ ለንግድ አገልግሎት አይውልም፡፡ ቀሪዎቹ ባለአምስትና ባለስምንት ወለል ሕንፃዎች የመጀመሪያው ወለላቸው ለንግድ አገልግሎት ይውላል፡፡ 

በዚህ አካባቢ ውስጥ የሚካሄደውን ግንባታ ከሚመሩት ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤቶች መካከል አንዱ የሆነውን ፕሮጀክት 13 የሚመሩት አቶ ወርቁ አበራ እንደገለጹት፣ በዚህ አካባቢ ከመኖሪያ ቤቶች ሌላ በሊዝ የሚተላለፉ መሬቶች፣ የትምህርት ተቋማት፣ የጤና ተቋማት፣ የቀላል ኢንዱስትሪ ቦታዎች፣ መዝናኛ ማዕከላትና የገበያ ማዕከላት የሚገነቡባቸው ቦታዎች ይኖሩዋቸዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት አንድ ትምህርት ቤትና ጤና ጣቢያ እየተገነባ መሆኑን አቶ ወርቁ ገልጸዋል፡፡ 

ጥር 28 ቀን 2006 ዓ.ም. በሥፍራው የተገኘው የጋዜጠኞች ቡድን የኮንዶሚኒየም ቤቶቹ ከ85 በመቶ በላይ መጠናቀቃቸው ተገልጾላቸዋል፡፡ 

ነገር ግን ከዚህ ቀደም ባሉት አሠራሮች 80 በመቶ ሲጠናቀቅ፣ ዕጣ የማውጣት ሥራ የሚካሄድ በመሆኑና ይኼኛው ፕሮጀክት ግን ግንባታው ከ85 በመቶ በላይ ቢጠናቀቅም፣ ዕጣ ያልወጣበትን ምክንያት ለማወቅ ለአዲስ አበባ ቤቶች ግንባታ ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ኃላፊ አቶ ካሳ ወልደ ሰንበት ከሪፖርተር ጥያቄ ቀርቦላቸዋል፡፡

አቶ ካሳ እንደሚሉት፣ ለየካ አባዶ ቤቶች ዕጣ ያልወጣው የሚያስፈልጉ የመሠረተ ልማት ግንባታዎች እንዲጠናቀቁ በማሰብ ነው፡፡ የመሠረተ ልማት ግንባታዎች ሳይጠናቀቁ ነዋሪዎች ቤቶቹን ቢረከቡ ችግሮች ስለሚፈጠር የመንገድ ግንባታ፣ የኤሌክትሪክና የውኃ መስመር ግንባታዎች መጠናቀቅ ስላለባቸው ነው ብለዋል፡፡ አቶ ካሳ ጨምረው እንደገለጹት፣ እነዚህ ግንባታዎች እየተፋጠኑ በመሆኑ በቅርቡ ዕጣ ይወጣላቸዋል፡፡

ሌላው በአዲስ አበባ ከተማ ከተገነቡ የኮንዶሚኒየም ቤቶች ትልቁ የሆነው ቦሌ አራብሳ ነው፡፡ ቦሌ አራብሳ በሰሚት ኮንዶሚኒየምና በአያት ኮንዶሚኒየም መሀል ላይ የሚገኝ ነው፡፡ 

በዚህ የግንባታ አካባቢ 674 የኮንዶሚኒየም ሕንፃዎች እየተገነቡ ይገኛሉ፡፡ እነዚህ ሕንፃዎች በአጠቃላይ 20,033 ቤቶች ሲኖራቸው፣ 392 ሕንፃዎች ዝቅተኛ ገቢ ላላቸው የኅብረተሰብ ክፍሎች የሚገነቡት የ10/90 ፕሮግራም ሕንፃዎች ናቸው፡፡ 

የግንባታ ቀጣናው እጅግ ሰፊና ከመኖሪያ ቤት በተጨማሪ ለተለያዩ አገልግሎቶች የሚውሉ ግንባታዎችን ያቅፋል ተብሏል፡፡ በዚህ የግንባታ አካባቢ እንደ የካ አባዶ ሁሉ ባለሦስት ወለል፣ ባለአምስት ወለልና ባለስምንት ወለል ሕንፃዎች ናቸው እየተገነቡ የሚገኙት፡፡   

በዚህ የግንባታ አካባቢ አስቸጋሪ ሁኔታ ፈጥረዋል ከተባሉ ችግሮች መካከል የኤሌክትሪክና የውኃ መስመር ዝርጋታ መጓተቱ ነው፡፡

ግንባታውን በማካሄድ ላይ የሚገኙ ኮንትራክተሮች የመስመሮቹ አለመዘርጋት ፈታኝ እንደሆነባቸውና በአፋጣኝ ካልተዘረጉ የቤቶቹ ግንባታ በተያዘለት የጊዜ ገደብ ማጠናቀቅ እንደሚያስቸግራቸው ገልጸዋል፡፡

ይህንን ችግር ለመፍታት በምክትል ከንቲባ አቶ አባተ ስጦታ የሚመራ ‹‹ኮማንድ ፖስት›› ከሚመለከታቸው አካላት ጋር እየተነጋገረና ችግሩንም ለመፍታት ጥረት እያደረገ ነው ተብሏል፡፡

በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እስካሁን ድረስ 108,482 ኮንዶሚኒየም ቤቶች ለተጠቃሚዎች መተላለፋቸው ይነገራል፡፡ ነገር ግን በቅርቡ ይፋ በተደረገው አራት ዓይነት የቤቶች ፕሮግራም አንድ ሚሊዮን ያህል ሰዎች ተመዝግበው ቤታቸውን በመጠባበቅ ላይ ይገኛሉ፡፡ በዚህ ዓመት 98 ሺሕ ቤቶች በመገንባት ላይ ሲሆኑ፣ አስተዳደሩ ዘንድሮ ለመገንባት ካቀዳቸው 65 ሺሕ ቤቶች ተጨማሪ 50 ሺሕ ቤቶችን ለመገንባት ዝግጅቱን አጠናቋል፡፡

አቶ ካሳ እንደገለጹት፣ ከሁለት ሳምንት በኋላ 50 ሺሕ ቤቶች ለመገንባት የመሠረት ድንጋይ ይጣላል፡፡ ለአዳዲሶቹ ግንባታዎች የቦታ ዝግጅት መጠናቀቁንና ከ50 ሺሕ በላይ ቤቶች ለመገንባት ከ500 ሔክታር በላይ መሬት የተመደበ መሆኑ ታውቋል፡፡ 

 

የግብፅ የውኃ ሀብት ሚኒስትር ኢትዮጵያ ይመጣሉ ተብሎ ይጠበቃል

$
0
0
የግብፅ የውኃ ሀብት ሚኒስትር ኢትዮጵያ ይመጣሉ ተብሎ ይጠበቃል

-ግብፅ የኢትዮጵያ ግድብ ቅርሶቼን ለአደጋ ያጋልጣል እያለች ነው

የታላቁ ህዳሴ ግድብን በተመለከተ የጠራ አቋም መያዝ የተቸገሩት የግብፅ ባለሥልጣናት በግድቡ ላይ ምንም ዓይነት ውይይት እንደማያደርጉ ካሳወቁ በኋላ፣ ሐሳባቸውን በመቀየር ውይይት በመምረጣቸው ምክንያት በዚህ ሳምንት የግብፅ የውኃ ሀብት ሚኒስትር አዲስ አበባ ይገባሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

እ.ኤ.አ. ጃንዋሪ 4 ቀን 2014 በሱዳን ዋና ከተማ ካርቱም የኢትዮጵያ፣ የግብፅና የሱዳን የውኃ ሚኒስትሮች የኢትዮጵያን የህዳሴ ግድብ በተመለከተ ለሦስተኛ ጊዜ ለመምከር ቢገናኙም ውይይቱ ሳይስማሙ መበተኑ ይታወሳል፡፡ ከዚህ በኋላ ውይይት እንደበቃቸው በተደጋጋሚና በተለያዩ መንገዶች የግብፅ ባለሥልጣናት ቢናገሩም፣ የውኃ ሀብትና የመስኖ ሚኒስትሩ መሐመድ አብዱል ሙታሊብ ከኢትዮጵያ አቻቸው ጋር ለመነጋገር ጥያቄ አቅርበዋል፡፡ 

የውኃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስቴር የወሰንና ወሰን ተሻጋሪ ወንዞች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ፈቅአህመድ ነጋሽ የግብፅ ሚኒስትር ከኢትዮጵያ አቻቸው ጋር ለመነጋገር ያቀረቡት ጥያቄ ተቀባይነት አግኝቶ የጉብኝት ፈቃድ እንደተሰጣቸው ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ በዚህ የጉብኝት ፈቃድ መሠረት በዚህ ሳምንት አዲስ አበባ በመምጣት ከሚኒስትሩ አቶ አለማየሁ ተገኑ ጋር ይወያያሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በተጨማሪም ሌሎች የመንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናትንም እንደሚያነጋግሩ ታውቋል፡፡

ይሁን እንጂ የግብፅ ባለሥልጣናት የህዳሴውን ግድብ በተመለከተ እያሳዩት የሚገኘው ተለዋዋጭ አቋም እንደበፊቱ ላለመቀጠሉ እርግጠኛ መሆን እንደማይቻል፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ሰሞኑን መናገራቸው ይታወሳል፡፡ 

የግብፅ መንግሥት የህዳሴውን ግድብ ግንባታ በተመለከተ የተለያዩ ነጥቦችን በማንሳት ከኢትዮጵያና ከሱዳን መንግሥታት ጋር ለሦስት ጊዜያት ቢወያይም፣ በውይይቶቹ የግብፅን መንግሥት አቋም ለይቶ ማወቅ አለመቻሉን የኢትዮጵያ መንግሥት ባለሥልጣናት ያስረዳሉ፡፡

በተለይ በውይይቱ የተሳተፉ የመንግሥት ተወካዮች የግብፅ መንግሥት በውይይት አማካይነት መግባባት ላይ ከመድረስ ይልቅ የተደበቀ አጀንዳ እንዳለው ይገምታሉ፡፡ ይህንን የግብፅ የተደበቀ አጀንዳ ከሚጠረጥሩ የኢትዮጵያ መንግሥት ተወካዮች መካከል አቶ ፈቅአህመድ ነጋሽ ይገኙበታል፡፡ እንደሳቸው ገለጻ የግብፅ መንግሥት በህዳሴው ግድብ ላይ ያለውን ጥርት ያለ አቋም ማወቅ አስቸጋሪ ነው፡፡ ምናልባትም በቅርቡ በግብፅ በፀደቀው አዲሱ ሕገ መንግሥት መሠረት የሚመሠረተው መንግሥት ይህንን ችግር ይፈታዋል ብለው ይገምታሉ፡፡

በአጠቃላይ ግብፅ የህዳሴውን ግድብም ሆነ ተያያዥ ጉዳዮችን አስመልክቶ ከዚህ በኋላ ያላት ብቸኛ አማራጭ ከተፋሰሱ በተለይም ከላይኛው ተፋሰስ አገሮች ጋር መወያየት ብቻ ነው ሲሉ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ ‹‹ውይይት ሲባልም እውነተኛ ወይይት መሆን አለበት፤›› በማለት ያስረዳሉ፡፡ 

በሌላ በኩል የግብፅ የመረጃ አገልግሎት ‹‹የግብፅ የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ በአፍሪካ የገጠሙት ፈተናዎች›› በሚል ባደረገው ጥናት ያቀረባቸው ፈተናዎች በዋናነት የሚያጠነጥኑት በውኃ ፖለቲካ ላይ ነው፡፡ በዚህም የተነሳ ግብፅ የዓባይ ወንዝ ተጋሪ ከሆኑ የአፍሪካ አገሮች ማለትም ከኢትዮጵያ፣ ከኡጋንዳ፣ ሩዋንዳ፣ ከታንዛኒያ፣ ከኬንያና ከብሩንዲ ፈተና ተጋርጦባታል ይላል፡፡

ይህንን ችግር ለመቅረፍ የግብፅ መንግሥት መከተል ይገባዋል በማለት ከሚያስቀምጣቸው የመፍትሔ ሐሳቦች መካከል፣ ግብፅ ከዚህ ቀደም የዓባይ ውኃን አስመልክቶ ከምታንፀባርቀው አቋም የተለየና የውኃ መጋራትን መሠረት ያደረገ አቀራረብ መሆን ይገባዋል ይላል፡፡

በተጨማሪም የአፍሪካ አገሮች በተለይም የዓባይ ተፋሰስ አገሮች ተማሪዎች በግብፅ የከፍተኛ ትምህርት ዕድል (ስኮላርሺፕ) እንዲያገኙ ማድረግና የባህል ማዕከላትን በተፋሰሱ አገሮች በመክፈት ግብፅን ከአፍሪካውያን ጋር ማቀራረብ ተገቢ ነው በማለት ያስረዳል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ የግብፅ ጥንታዊ ቅርሶች ሚኒስትር መሐመድ ኢብራሂም ሰሞኑን የኢትዮጵያ ታላቁ የህዳሴ ግድብ በግብፅ ላይ ሊያመጣ ስለሚችለው ጥፋት የተለየ አዲስ ሐሳብ ለመገናኛ ብዙኃን ተናግረዋል፡፡ ከዚህ ቀደም ግድቡ የግብፅን የውኃ መጠን ስለሚቀንስ ለግብፅ የብሔራዊ ደኅንነት ጉዳይ መሆኑን ባለሥልጣናቱ ሲገልጹ ቆይተዋል፡፡ የቅርስ ሚኒስትሩ ደግሞ በህዳሴ ግድቡ ግንባታ ምክንያት የግብፅ ጥንታዊ ቅርሶች (ፒራሚዶችን ጨምሮ) ለአደጋ ያጋልጣቸዋል ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ታላቁ የህዳሴ ግድብ ዕውን መሆን የከርሰ ምድር ውኃ መጠንን በመቀነስ የመሬት አለመረጋጋት (መንሸራተትን) የሚፈጥር በመሆኑ፣ የግብፅ ጥንታዊ ቅርሶች አደጋ ላይ ሊወድቁ ይችላሉ በማለት አዲስ ሐሳብ ይዘው ቀርበዋል፡፡ 

የግብፅ ባለሥልጣናት በተደጋጋሚ የተለያዩ ምክንያቶችን በመደርደር የሚገኙ ሲሆን፣ የአሁኑ በጥንታዊ ቅርሶች ላይ አደጋ ተደቅኗል የሚለው ሐሳባቸው ብዙዎችን አስገርሟል፡፡ ዴይሊ ኒውስ በተሰኘው ድረ ገጽ ላይ አስተያየታቸውን የሰጡ በርካታ ኢትዮጵያውያን የግብፅ ባለሥልጣናትን ተለዋዋጭ አቋም አውግዘዋል፡፡ በዓባይ ወንዝ ፍትሐዊ ተጠቃነሚት ላይ ማተኮር ሲገባቸው ግድቡን በጠላትነት መመልከታቸው ተቀባይነት እንደሌለው በማስረዳት፣ አሁንም ለድርድርና ለውይይት ራሳቸውን ከማዘጋጀት ውጪ ሌላው ተግባራቸው ተቀባይነት እንደሌለው ነግረዋቸዋል፡፡

የግብፅ ባለሥልጣናት ለኢትዮጵያ ዕርዳታና ብድር በማስከልከል፣ የግድቡን ግንባታ ጉዳይ ወደ ተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ለመውሰድ መነሳታቸው አልበቃ ብሎ፣ አንዴ የግንባታ መጠኑ እንዲቀንስ ሌላ ጊዜ ደግሞ በቅርሶች ላይ አደጋ ያደርሳል ማለታቸው ተወግዟል፡፡ ታላቁ የአስዋን ግድብ ሲገነባ ለምን ይህ ጥያቄ አልተነሳም በማለት የሞገቱት ኢትዮጵያውያን፣ ይህ ተለዋዋጭ የግብፅ ባለሥልጣናት አቋም አደብ እንዲገዛም ጠይቀዋል፡፡

ባለፈው ሳምንት 45 አባላት ያሉት የዲፕሎማሲ ቡድን አዲስ አበባ ለመምጣት ከባለሥልጣናትና ከተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ጋር በመገናኘት ውይይት አድርጓል፡፡ አሁን ደግሞ የውኃ ሀብትና የመስኖ ሚኒስትሩ መሐመድ አብዱል ሙታሊብ አዲስ አበባ በመምጣት በግድቡ ላይ ለመነጋገር ጥያቄ አቅርበው ተፈቅዶላቸዋል፡፡ ግብፆች ተለዋዋጭ በሆነው አቋማቸው እስከመቼ የተለያዩ ሐሳቦችን ያራምዳሉ የሚሉ የመስኩ ባለሙያዎች፣ የኢትዮጵያ መንግሥት እያንዳንዱን የግብፆች ዕርምጃ በጥንቃቄና በትኩረት መከታተል እንዳለበት ያሳስባሉ፡፡

መንግሥት በአገሪቱ ውስጥ በተለይ በዓባይ ጉዳይ ብሔራዊ መግባባት እንዲፈጠር በማድረግ፣ በመስኩ ዕውቀት ያላቸውን ባለሙያዎችና ምሁራን በማሳተፍ፣ በየደረጃው የውይይት መድረኮችን በማዘጋጀት የአገሪቱን ግልጽ አቋም ማሳወቅ እንደሚኖርበት የሚጠይቁ ብዙዎች ናቸው፡፡ በተለይም በዩኒቨርሲቲዎችና በተለያዩ ተቋማት ውስጥ የሚገኙ ምሁራን በዚህ ብሔራዊ ጉዳይ ላይ አስተዋጽኦ ማድረግ ሲገባቸው ብዙዎቹ ዝምታ መምረጣቸውንም ይተቻሉ፡፡

የአገሪቱ ሕዝብ፣ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ፣ የውጭና የአገር ውስጥ ሚዲያዎች የታላቁ ህዳሴ ግድብ በግብፅ ባለሥልጣናት ለምን ተቃውሞ እንደሚቀርብበት፣ የግድቡ ግንባታን የጥራት ደረጃና ሙሉ ምሥል የሚያሳይ መረጃ የማቅረብ ኃላፊነት የመንግሥት በመሆኑ ትኩረት እንዲደረግበት በአፅንኦት ያሳስባሉ፡፡ ሰሞኑን የግብፅ ባለሥልጣናት ሱዳንን ከኢትዮጵያ ለመነጠል የጀመሩትን ዘመቻና ተለዋዋጭ አቋማቸውን በተጨባጭ ማጋለጥ እንዲያስችለው ዘርፈ ብዙ ዝግጅት ለማድረግ ዜጎችን በምልዓት ማሳተፍ አለበት ሲሉ ያስረዳሉ፡፡ 

 


ንግድ ባንክ 16.4 ቢሊዮን ብር ተቀማጭ ሰበሰብኩኝ አለ

$
0
0
ንግድ ባንክ 16.4 ቢሊዮን ብር ተቀማጭ ሰበሰብኩኝ አለ

-4.6 ቢሊዮን ብር ያልተጣራ ትርፍ ማግኘቱን ገለጸ

-በደቡብ ሱዳን የደረሰበትን ዝርፊያ ከመግለጽ ተቆጥቧል

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እ.ኤ.አ. ከጁላይ 1 ቀን 2013 እስከ ዲሴምበር 31 ቀን 2013 ድረስ ባለው የስድስት ወራት የሥራ አፈጻጸም፣ 9.8 ቢሊዮን ብር ተቀማጭ ገንዘብ ለመሰብሰብ አቅዶ፣ 16.4 ቢሊዮን ብር (166.9 በመቶ) መሰብሰቡን አስታወቀ፡፡

ባንኩ የስድስት ወራት የሥራ አፈጻጸሙን በሚመለከት ለመገናኛ ብዙኃን ባለፈው ዓርብ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ እንደገለጸው፣ የቁጠባ ባህልን በኅብረተሰቡ ውስጥ በማጐልበትና የአገር ውስጥ ቁጠባ መጠን እንዲያድግ መጠነ ሰፊ ሥራዎችን በማከናወኑ፣ በግማሽ ዓመቱ ለመሰብሰብ አቅዶት ከነበረው በእጥፍ የሚገመት ተቀማጭ ገንዘብ መሰብሰቡን ይፋ አድርጓል፡፡

ባንኩ ለግሉ ዘርፍ ትኩረት በመስጠት ቅድሚያ ለሚሰጣቸው መስኮች ማለትም ግብርና፣ ማኑፋክቸሪንግና የወጪ ንግድ 7.3 ቢሊዮን ብር ብድር ማቅረብ መቻሉን፣ የባንኩ የቢዝነስ ዴቨሎፕመንት የሥራ ሒደት ኃላፊ አቶ ይስሐቅ መንገሻና የኮሙዩኒኬሽን ሥራ አስኪያጅ አቶ ኤፍሬም መኩሪያ በጋራ በሰጡት መግለጫ አስረድተዋል፡፡ ባንኩ በግማሽ ዓመቱ የሰበሰበው የብድር መጠን 18.7 ቢሊዮን ብር መሆኑንና ያበደረው የገንዘብ መጠን ደግሞ 35.3 ቢሊዮን ብር እንደሆነ ኃላፊዎቹ አክለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በግማሽ ዓመቱ 7.8 ቢሊዮን ብር ገቢ ማግኘቱና ያልተጣራ 4.6 ቢሊዮን ብር ማትረፉም ተነግሯል፡፡ የውጭ ምንዛሪን በሚመለከት ባንኩ 2.6 ቢሊዮን ዶላር ለማግኘት አቅዶ የነበረ ቢሆንም፣ ያገኘው ግን 2.3 ቢሊዮን ዶላር መሆኑንም ኃላፊዎቹ ጠቁመዋል፡፡

በውጭ ምንዛሪም 3.27 ቢሊዮን ዶላር ክፍያዎች መፈጸማቸውንና ለግሉ ዘርፍ ለጥሬ ዕቃ፣ ለማኑፋክቸሪንግ፣ ለካፒታል ዕቃዎችና ለሕክምና መገልገያ መሣሪያዎች ባንኩ 754 ሚሊዮን ዶላር ክፍያ መፈጸሙም ተጠቅሷል፡፡ 

ንግድ ባንክ ሴት ቆጣቢዎችን ለማፍራት ከንግድ ተቋማት ጋር እየተፈራረመ መሆኑንና መልካም ውጤት መገኘቱን ኃላፊዎቹ በመግለጫቸው ጠቁመዋል፡፡ 

የኢትዮጵያ ሕዝብ ብዛት ከ80 ሚሊዮን በላይ መሆኑ የሚታወቅ ቢሆንም፣ ወደ ባንክ (አጠቃላይ ንግድ ባንኮች) የመጣው የሕዝብ ብዛት 15 ሚሊዮን አለመድረሱን የገለጹት ኃላፊዎቹ፣ ባንኩ ባደረገው ጥናት በተለይ ሴት ቆጣቢዎች እጅግ በጣም ትንሽ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡

በመሆኑም ባንኩ የተለያዩ አገልግሎት ሰጪዎች ማለትም ከሱፐርማርኬቶች፣ ከውበት ሳሎኖች፣ ከቤትና ቢሮ ዕቃ አቅራቢዎች፣ ሀኪም ቤቶችና ከሌሎችም ጋር በመነጋገርና ከአገልግሎት ሰጪ ድርጅቶች ጋር በመፈራረም ለሴቶች ልዩ የመቆጠቢያ ደብተርና ካርድ በመስጠት እንዲገበያዩ ለማድረግ ሥራ መጀመሩን ኃላፊዎቹ ገልጸዋል፡፡ አገልግሎት ሰጪዎቹ በሚሸጡት ዕቃ ላይ እስከ 40 በመቶ የሚደርስ ቅናሽ እንደሚያደርጉም አክለዋል፡፡ ዋናው ቁም ነገር ግን ከሚገዙት ወይም ከሚያገኙት አገልግሎት ቅናሽ እንዲያገኙ ሳይሆን፣ ቁጠባን እንዲለምዱና ባንኩ በሚሰጣቸው ጠቀም ያለ ወለድ ተጠቃሚ ለማድረግ መሆኑን አውስተዋል፡፡

በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በተለያዩ ጊዜያት ዓይነታቸውን እየቀያየሩ የሚፈጸሙ ዝርፊያዎችን በሚመለከት የተጠየቁት ኃላፊዎቹ፣ ‹‹ንግድ ባንክ የሚቀጥራቸው ሠራተኞች ብቃት ያላቸው ቢሆኑም የተለያዩ ሥልጠናዎች እንዲያገኙ ይደረጋል፡፡ ከሙያና ከሥነ ምግባር ጋር የተገናኙ ሥልጠናዎች በተለያዩ ጊዜያት ይሰጣሉ፡፡ ነገር ግን አንዳንድ ሥነ ምግባር የጐደለው ሠራተኛ አልፎ አልፎ ያጋጥማል፡፡ ማጭበርበሮችም ይፈጸማሉ፡፡ ይኼ ግን በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ላይ ብቻ የሚፈጸም ሳይሆን፣ በዓለም ደረጃ ባሉ የፋይናንስ ተቋማት ላይም የሚያጋጥም ነው፡፡ ችግሮችን እየነቀስንና እያስተማርን፣ አስተዳደራዊ ዕርምጃ ከመውሰድ ጀምሮ በሕግ እስከመጠየቅ ድረስ እየሠራንና አሠራራችንን በቴክኖሎጂ በመቀየር ጠንክረን እየሠራን ነው፤›› ብለዋል፡፡ 

ያልተወራረዱ ሒሳቦችን በሚመለከት ለተነሳላቸው ጥያቄ፣ ትኩረት ሰጥተው እየሠሩበት እንደሆነ ከመግለጽ ውጪ ዝርዝር ምላሽ ከመስጠት ተቆጥበዋል፡፡ የተበላሸ ብድርን በሚመለከት በተደጋጋሚ ጥያቄ ቢነሳም ኃላፊዎቹ ምላሽ ሳይሰጡበት አልፈዋል፡፡

ባንኩ ተቀማጭ ሒሳቦችን ለማሰባሰብ የኅብረተሰቡን ግንዛቤ ለማስጨበጥ በሚያደርገው ትግል ከሚያጋጥመው ችግር በተጨማሪ ቅርንጫፎቹን በእጥፍና ከዚያም በላይ ለማስፋፋት፣ የቴሌ መሠረተ ልማት አለመሟላት ሌላው ችግር መሆኑን ኃላፊዎቹ አስረድተዋል፡፡ 

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በደቡብ ሱዳን ከከፈታቸው ቅርንጫፎቹ በተለይ ማላካል ከተማ በሚገኘው ቅርንጫፍ ላይ ተፈጽማል ስለተባለው ዝርፊያ የተጠየቁት ኃላፊዎቹ፣ ‹‹ዝርፊያ ሊኖር ይችላል፡፡ ሠራተኛ ግን ምንም አልሆነብንም፡፡ ለማንኛውም ግን መረጃ ስናገኝ ወደፊት ይገለጻል፡፡ በወሬ ደረጃ ስለሆነ መረጃው የለንም፤›› ከማለት ውጪ ግልጽ የሆነና የተፍታታ ማብራሪያ ለመስጠት አልቻሉም፡፡

የ10/90፣ የ20/80 እና የ40/60 የኮንዶሚኒየም ቤት ቆጣቢዎችን በሚመለከት ለተነሳላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ፣ በሦስቱም የቤት ፕሮግራሞች ላይ የተመዘገቡ ዜጐች ቁጠባ እየጨመረ መሆኑን ኃላፊዎቹ አስረድተዋል፡፡ እንዲያውም አንዳንዶቹ ቆጣቢዎች በየወሩ እንዲቆጥቡ ከተተመነላቸው የገንዘብ መጠን በላይ እየቆጠቡ መሆኑንም አክለዋል፡፡ እስካሁን ስላላጋጠመ እንጂ መቆጠብ ያቋረጠ ወይም በማመልከቻ ቁጠባውን መቀጠል የማይፈልግ ካለ፣ ከቤቶቹ ፕሮግራም ተሰርዞ የቆጠበው ገንዘብ ወደ መደበኛ ቁጠባ እንደሚዛወርለትም ኃላፊዎቹ አስረድተዋል፡፡ ይህንንም በተመለከተ እስካሁን የተሰበሰበውን የገንዘብ መጠን መግለጽ አልቻሉም፡፡ 

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጠቅላላ ሀብቱ 210 ቢሊዮን ብር መድረሱን፣ በግማሽ ዓመቱ 85 ቅርንጫፎችን ከመክፈቱ ጋር ተደምሮ 780 ቅርንጫፎች ያሉት መሆኑን፣ ከስድስት ሚሊዮን በላይ ደንበኞች ያላቸው 470 ቅርንጫፎች በኢንተግሬትድ ኮር ባንኪንግ ሶሉዩሺን ቴክኖሎጂ እርስ በርሳቸው የተሳሰሩ መሆናቸውን ኃላፊዎቹ አስረድተዋል፡፡ 368 የኤቲኤምና 367 የሽያጭ ማዕከል ማሽኖች አገልግሎት እየሰጡ መሆኑንና የባንኩ የሰው ኃይል 18,035 መድረሱንም አክለዋል፡፡

 

 

ሰበር ዜና : የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላንን የጠለፈው ረዳት አብራሪ በቁጥጥር ሥር ዋለ

$
0
0
ሰበር ዜና : የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላንን የጠለፈው ረዳት አብራሪ በቁጥጥር ሥር ዋለ

ሰኞ ማለዳ (የካቲት 10) ከአዲስ አበባ ወደ ሮም ሲያመራ የነበረውን የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላን ጠልፎ ጄኔቭ እንዲያርፍ ያስገደደው የአውሮፕላኑ ረዳት አብራሪ በጄኔቭ ፖሊስ በቁጥጥር ሥር ዋለ፡፡

የበረራ ቁጥር ET 702 አውሮፕላን የጠለፈው ረዳት አብራሪ በስም ባይጠቀስም ተገዶ ባረፈው አውሮፕላን ውስጥ የሚገኙት ተሳፋሪዎችም ሆኑ የአውሮፕላኑ ሠራተኞች በመልካም ሁኔታ ላይ እንደሚገኙ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በድረ ገጹ አስታውቋል፡፡
ሮይተርስ ቀደም ብሎ ያነጋገራቸው የኢትዮጵያ መንግሥት ቃል አቀባይ ሬድዋን ሁሴን አውሮፕላኑ በሱዳን መዲና ካርቱም በኩል ማለፉንና ምናልባትም ጠላፊው ወይም ጠላፊዎቹ ከዚያው ሳይሳፈሩ እንዳልቀረ ተናግረው ነበር፡፡ መጨረሻ ላይ በተገኘው መረጃ ጠላፊው ረዳት አብራሪው መሆኑ ተረጋግጧል፡፡

ሟቾችን መለየት ያልተቻለበት የተሽከርካሪ አደጋ ደረሰ

$
0
0
ሟቾችን መለየት ያልተቻለበት የተሽከርካሪ አደጋ ደረሰ

የካቲት 1 ቀን 2006 ዓ.ም. ከአዲስ አበባ ወደ አዳማ (ናዝሬት) በሚጓዘው ሚኒባስ ውስጥ 12 ሰዎች ተሳፍረዋል፡፡

በዚየን ቀን ማለዳ ለተለያዩ ሥራዎችና ማኅበራዊ ጉዳዮች ወደ አዲስ አበባ የመጡ ተሳፋሪዎች፣ ከቤተሰቦቻቸው ተመልሰው ለመገናኘት የ99 ኪሎ ሜትር ርቀት አልገፋ ብሏቸዋል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ቀኑ መምሸቱ ነበር፡፡

ባለቤታቸውን በቀበሩ በ12ኛው ቀን የጓደኛቸው ወንድም መሞቱን ሰምተው ለቀብር ወደ አዲስ አበባ የመጡት ወ/ሮ ርግበ መብራህቱም ከተሳፋሪዎቹ አንዷ ናቸው፡፡ በሐዘን የተጐዱ ልጆቻቸውንና የሐዘናቸው ተካፋይ የሆኑ ዘመዶቻቸውን ለመቀላቀል እሳቸውም ልባቸው ተሰቅሏል፡፡ ከምሽቱ አንድ ሰዓት ካለፈ በኋላ አዲስ አበባን ለቆ ወደ አዳማ ያመራው ሚኒባስ፣ የመጨረሻ ፍጥነቱን ተጠቅሞ መብረሩን ተያይዞታል፡፡ እንኳን ምሽትን ተገን አድርጐ ቀርቶ ቀንም ቢሆን ‹‹ኧረ ቀስ በሉ›› ቢባሉ ከማይሰሙ አሽከርካሪዎች አንዱ የሆነው የሚኒባሱ ሾፌር፣ የሚኒባሱን ሙዚቃ ከፍ አድርጐ በመልቀቅ በከፍተኛ ፍጥነት ይነዳል፡፡ የተለያዩ ተሽከርካሪዎችን በማለፍ ገላን፣ ዱከም፣ ቢሾፍቱንና ሞጆን ያለፈው ሚኒባስ መጨረሻ ግን አዳማ አልደረሰም፡፡ ሞጆን እንዳለፈ አንድ መጠምዘዢያ ኩርባ ላይ ሲደርስ፣ ከአዳማ ወደ አዲስ አበባ መስመሩን ይዞ ከሚመጣ ኤንትሬ ተሳቧ ጋር ተገናኘ፡፡

ሚኒባሱ ይሄድበት የነበረውን ፍጥነት ቀንሶ ወይም አቁሞ ለማሳለፍ እንደማይችል ያወቀው አሽከርካሪ፣ ደርቦ ማለፍ የመጨረሻው አማራጭ መሆኑን ተረዳ፡፡ በመሆኑም ፍጥነቱን ሳይቀንስ ደርቦ ለማለፍ ሲሞክር የተሳቢው ስፖንዳ ሲመታው ሙሉ በሙሉ በተሳቢው ውስጥ ተቀረቀረ፡፡ ሚኒባሱ አሳፍሯቸው ከነበሩት 12 ተሳፋሪዎች መካከል አንድ ዕድለኛ ተሳፋሪ ከጋቢና ተስፈንጥሮ በመውደቁ ትንሽ ጉዳት ደርሶበት ሲተርፍ፣ ሌሎች ሁለት ደግሞ ከባድ ጉዳት ደርሳባቸው ተረፉ፡፡ አሽከርካሪውን ጨምሮ ስምንት ተሳፋሪዎች ተጨፈላልቀው ሕይወታቸው አልፏል፡፡ በባላቸው ሐዘን ውስጥ የከረሙት ወ/ሮ ርግበ ብቻ አካላቸው ሳይቆራረጥ ነፍሳቸው ከሥጋቸው ተለይቶ ሲገኙ፣ የቀሪዎቹን ሰባት ማንነት መለየት ባለመቻሉ የአዳማ ማዘጋጃ ቤት ሊቀበራቸው ተገዷል፡፡ በምሥሉ ላይ አደጋውን ያደረሰው ሚኒባስ ከጥቅም ውጪ ሆኖ ሲታይ፣ ሟች ወ/ሮ ርግበ መብራህቱ እኚህ ነበሩ፡፡ (በታምሩ ጽጌ)

 

 

ፍትሕ ሚኒስቴር አክሰስ ሪል ስቴትን በተመለከተ ለመንግሥት ተቋማት ደብዳቤ ላከ

$
0
0

-የሪል ስቴት ደንበኞች ግራ ተጋብተናል ይላሉ

ከአክሰስ ሪል ስቴት አክሲዮን ማኅበር፣ ከሪል ስቴቱ ዋና ሥራ አስኪያጅና ቤት ለማሠራት ክፍያ ከፈጸሙ በርካታ ግለሰቦች ጋር በተገናኘ ፍትሕ ሚኒስቴር ለአራት የመንግሥት ከፍተኛ ተቋማት የጻፈው የጥንቃቄ መጠቆሚያና ማሳሰቢያ ደብዳቤ ላከ፡፡

የሪል ስቴቱ ደንበኞች ደግሞ የደብዳቤው መጻፍ ግራ እንዳገባቸው ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

በፍትሕ ሚኒስትሩ አቶ ጌታቸው አምባዬ ፊርማ ጥር 21 ቀን 2006 ዓ.ም. ወጪ የተደረገው ደብዳቤ ለፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት፣ ለንግድ ሚኒስቴር፣ ለሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ ጽሕፈት ቤትና ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር መሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ የተላከ ነው፡፡ 

ደብዳቤው፣ ‹‹በአክሰስ ሪል ስቴት አክሲዮን ማኅበርና በቀድሞው ሥራ አስኪያጅ አቶ ኤርሚያስ ጠቅል አመልጋ የተመዘገቡ ንብረቶችና ጉዳዮችን ይመለከታል›› ይልና፣ በማኅበሩና በአቶ ኤርሚያስ ከፍተኛ የሆኑ ሕገወጥ ሥራዎች መፈጸማቸውን ያስታውሳል፡፡

በመሆኑም መንግሥት ያጋጠሙትን ችግሮች መነሻ በማድረግ ለጉዳዩ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት ሁሉንም ወገኖች ያማከለ ውሳኔ መስጠት አስፈላጊ መሆኑን እንዳመነበት ደብዳቤው ይገልጻል፡፡

መንግሥት ውሳኔ ከመስጠቱ በፊት ግን የተለያዩ ወገኖች የራሳቸውን ጥቅምና ንብረት ለማስከበር ጉዳዮቻቸውን በተናጠል ፍርድ ቤት በማቅረብና ከማኅበሩ ጋር ያደረጉትን ውል በማፍረስ፣ የማኅበሩን ንብረቶች በማዘዋወር እንቅስቃሴ ውስጥ በመግባታቸው አሠራሩን የተወሳሰበ እያደረጉት መሆኑን የሚኒስቴሩ ደብዳቤ ያወሳል፡፡

መንግሥት ዘለቄታዊ መፍትሔ ለመስጠት ኮሚቴ አቋቁሞ በማጣራት ላይ በመሆኑ በማኅበሩ፣ በአቶ ኤርሚያስና በስማቸው የተመዘገቡ ንብረቶችና አክሲዮኖች ለሦስተኛ ወገን እንዳይሸጡ፣ እንዳይለወጡና እንዳይዘዋወሩ ጥንቃቄ እንዲደረግ ያሳስባል፡፡ ውሎች እንዳይፀድቁ፣ ፀድቀው የወጡ ውሎችና ስምምነቶችም ካሉ በመዝጋቢ አካላት በኩል ተፈጻሚ እንዳይሆኑ፣ በማኅበሩና በአቶ ኤርሚያስ ላይ በመታየት ላይ ስላሉ ክሶች፣ የተወሰኑና አፈጻጸም ላይ የደረሱ ካሉም ተጣርቶ በመንግሥት አማካይነት አቅጣጫ እስከሚቀመጥ እንዳይፀድቁና ባሉበት እንዲቆዩ ፍትሕ ሚኒስቴር በደብዳቤው አሳስቧል፡፡ 

አክሰስ ሪል ስቴትና ደንበኞቹ በመካከላቸው የፈጠሩት የኮንትራት ግንኙነት መሆኑን የሚገልጹ አስተያየት ሰጪዎች፣ በሁለቱ መካከል አለመግባባት ሲፈጠር በሽምግልና ወይም በፍርድ ቤት በኩል ችግሩን ሊፈቱት እንደሚችሉ ያስረዳሉ፡፡ 

ፍትሕ ሚኒስቴር ምናልባት ‹‹መሬት የመንግሥት ነው›› በሚል ጣልቃ ለመግባትና ነገሮችን ሌላ አቅጣጫ ለማስያዝ ካልሆነ በስተቀር፣ በሁለቱ ወገኖች መካከል ገብቶ መፍትሔ ሊሰጥ እንደማይችል ጉዳዩ ይመለከተናል የሚሉ ለሪፖርተር አስረድተዋል፡፡ ሚኒስቴሩ በሁለቱ ተዋዋይ ወገኖች መሀል መግባት እንደማይችልና ሥልጣኑም እንዳልሆነ አክለዋል፡፡

ፍትሕ ሚኒስቴር አስተዳደራዊ ክልከላ ሊያደርግ እንደማይችል የሚናገሩት አስተያየት ሰጪዎቹ፣ ሚኒስቴሩ ተመሳሳይ የማስፈጸም ሥልጣን ላላቸው ተቋማት የጐንዮሽ ትዕዛዝ የሚመስል ደብዳቤ በመጻፉ፣ የፍርድ ቤቶችን ነፃነት ከማሳጣቱም በላይ ደረጃቸውን ጠብቀው የሚሠሩበትን አሠራር ሊያበላሽ እንደሚችል ፍርኃታቸውን ገልጸዋል፡፡ 

 

 

 

ግንባታቸው ያላለቀ ሆቴሎችን የገዛው የዱባይ ኩባንያ በአፋጣኝ እንዲያጠናቅቅ ተጠየቀ

$
0
0
ግንባታቸው ያላለቀ ሆቴሎችን የገዛው የዱባይ ኩባንያ በአፋጣኝ እንዲያጠናቅቅ ተጠየቀ

አል ካራፊና ልጆቹ የገነባቸውን ያላለቁ ሆቴሎች የገዛው የዱባይ ኩባንያ ሆቴሎቹን በአፋጣኝ ገንብቶ እንዲያጠናቅቅ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጠየቀ፡፡

ላለፉት ሦስት ዓመታት ግንባታቸው ተቋርጦ የሚገኙት ሁለት ሆቴሎች ጉዳይ ያሳሰበው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር፣ ለሆቴሎቹ የቀድሞ ባለቤት አል ካራፊና ልጆቹ ኩባንያ ተደጋጋሚ ጥያቄ ቢያቀርብም ምላሽ አለማግኘቱን ምንጮች ገልጸዋል፡፡ 

በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ከመስቀል አደባባይ ፊት ለፊት የሚገኙት ባለሦስት ኮከቡ ሆቴል አይቢስና ባለአራት ኮከብ ሆቴል የሆነው ኖቮቴል በአጭር ጊዜ ውስጥ ግንባታቸው ቢፋጠንም፣ ላለፉት ሦስት ዓመታት ግን ግንባታቸው በመቋረጡ በጅምር እንዳሉ ናቸው፡፡ 

የሁለቱ ሆቴሎች ግንባታ በጅምር የቀረበት ምክንያት ማብራሪያ ያልቀረበለት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር፣ ግንባታው የተቋረጠበት ምክንያት እንዲብራራለትና የተቋረጠው ግንባታም በአስቸኳይ እንዲቀጥል በተደጋጋሚ ለቀድሞ ባለቤቱ በደብዳቤ ጥያቄ ቢያቀርብም ምላሽ አለማግኘቱን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ 

ምንጮች እንደገለጹት፣ በቅርቡ ሆቴሉን የገዛው ተቀማጭነቱን ዱባይ ያደረገው አልብዋርዲ ኩባንያ በቅርቡ ወደ ሥራ ለመግባት ዝግጅት እያደረገ ነው ተብሏል፡፡ አልብዋርዲ ሐያት ሆቴል ኢቨስትመንት በሚል ዓለም አቀፍ የንግድ ስያሜ 492 ሆቴሎችን እንደሚያስተዳድር ታውቋል፡፡ 

አል ካራፊና ልጆቹ ኩባንያ በ10,232 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ ደረጃቸውን የጠበቁ ሆቴሎችን በፍጥነት ገንብቶ ነበር፡፡ ነገር ግን የኩባንያው ከፍተኛ ባለድርሻ ናስር አል ካራፊ ከዚህ ዓለም በሞት በመለየታቸው ምክንያት የሆቴሉ ግንባታ ተቋርጣል፡፡ የኩባንያው ሌሎች የቤተሰብ ባለድርሻዎች በድጋሚ የኩባንያውን ቢዝነስ ዕቅድ በመከለስ ቅድሚያ የሚሰጧቸውን ፕሮጀክቶች መለየታቸው ይነገራል፡፡ ነገር ግን ለአዲስ አበባ የሆቴል ፕሮጀክት የኩባንያው ባለቤቶች ቅድሚያ ባለመስጠታቸው የተጀመረው ግንባታ መቋረጡ ተገልጿል፡፡ 

አል ካራፊና ልጆቹ ኩባንያ እነዚህን ሆቴሎች የፈረንሳይ ዓለም አቀፍ ኩባንያ በሆነው አኮር ሆቴል ስም ለማስተዳደር ዕቅድ ነበረው፡፡ 

በ1999 ዓ.ም. የተጀመረው የሆቴል ግንባታ በ38 ወራት ይጠናቀቃል የሚል ዕቅድ ቢኖረውም ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ ሆቴሉን የገዛው አዲሱ የዱባይ ኩባንያ በቅርቡ የስም ዝውውር ማካሄዱን የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ ጽሕፈት ቤት መረጃዎች ያረጋግጣሉ፡፡

          

 

Viewing all 1779 articles
Browse latest View live